ترجمة سورة الحديد

Sadiq and Sani - Amharic translation
ترجمة معاني سورة الحديد باللغة الأمهرية من كتاب Sadiq and Sani - Amharic translation .


በሰማያትና በምድር ያለው ሁሉ ለአላህ አሞገሰ፡፡ እርሱም ሁሉን አሸናፊው ጥበበኛው ነው፡፡

የሰማያትና የምድር ንግሥና የእርሱ ብቻ ነው፡፡ ሕያው ያደርጋል፤ ይገድላልም፡፡ እርሱም በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው፡፡

እርሱ ፊትም ያለ፣ ኋላም ቀሪ፣ ግልጽም፣ ስውርም ነው፡፡ እርሱም ነገሩን ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡

እርሱ ያ ሰማያትንና ምድርን በስድስት ቀናት ውስጥ የፈጠረ፤ ከዚያም በዙፋኑ ላይ (ስልጣኑ) የተደላደለ ነው፡፡ በምድር ውስጥ የሚገባውን፣ ከእርሷም የሚወጣውን፣ ከሰማይም የሚወርደውን በእርሷም ውስጥ የሚያርገውን ያውቃል፡፡ እርሱም የትም ብትኾኑ ከእናንተ ጋር ነው፡፡ አላህም የምትሠሩትን ሁሉ ተመልካች ነው፡፡

የሰማያትና የምድር ንግሥና የእርሱ ብቻ ነው፡፡ ነገሮችም (ሁሉ) ወደ አላህ ብቻ ይመለሳሉ፡፡

ሌሊትን በቀን ውስጥ ያስገባል፡፡ ቀንንም በሌሊት ውስጥ ያስገባል፡፡ እርሱም በልቦች ውስጥ የተደበቁትን ዐዋቂ ነወ፡፡

በአላህና በመልክተኛው እመኑ፡፡ (አላህ) በእርሱ ተተኪዎች ባደረጋችሁም ገንዘብ ለግሱ፡፡ እነዚያም ከእናንተ ውስጥ ያመኑትና የለገሱት ለእነርሱ ታላቅ ምንዳ አልላቸው፡፡

መልክተኛው በጌታችሁ እንድታምኑ የሚጠራችሁ ሲኾን (ጌታችሁ) ኪዳናችሁንም የያዘባችሁ ሲኾን በአላህ የማታምኑት ለእናንተ ምን አልላችሁ? የምታምኑ ብትኾኑ (ወደ እምነት ቸኩሉ)፡፡

እርሱ ከጨለማዎች ወደ ብርሃን ሊያወጣችሁ ያ ግልጾች የኾኑን አንቀጾች በበሪያው ላይ የሚያወርድ ነው፡፡ አላህም ለእናንተ በእርግጥ ርኅሩህ አዛኝ ነው፡፡

የሰማያትና የምድር ውርስ ለአላህ ሲኾን በአላህ መንገድ የማትለግሱትም ለእናንተ ምን አልላችሁ? ከእናንተ ውስጥ (መካን) ከመክፈት በፊት የለገሰና የተጋደለ ሰው (ከተከፈተች በኋላ ከለገሰና ከተጋደለ ጋር) አይስተካከልም፡፡ ከእነዚያ በኋላ ከለገሱትና ከተጋደሉት እነዚህ በደረጃ በጣም የላቁ ናቸው፡፡ ሁሉንም አላህ መልካሚቱን ተስፋ ቃል ገብቶላቸዋል፡፡ አላህም በምትሠሩት ሁሉ ውስጠ ዐዋቂ ነው፡፡

ያ ለአላህ መልካም ብድርን የሚያበድር ለእርሱም (አላህ) የሚያነባብርለት ሰው ማነው? ለእርሱም መልካም ምንዳ አልለው፡፡

ምእመናንንና ምእምናትን በስተፊቶቻቸው፣ በቀኞቻቸውም ብርሃናቸው የሚሮጥ ሲኾን በምታያቸው ቀን (ምንዳ አልላቸው)፡፡ ዛሬ ብስራታችሁ በውስጦቻቸው ዘውታሪዎች ስትኾኑ ከሥሮቻቸው ወንዞች የሚፈስሱባቸው ገነቶች ናቸው (ይባላሉ)፡፡ ይህ እርሱ ታላቁ ዕድል ነው፡፡

መናፍቃንና መናፍቃት ለእነዚያ ለአመኑት «ተመልከቱን፤ ከብርሃናችሁ እናበራለንና» የሚሉበትን ቀን (አስታውስ)፡፡ «ወደ ኋላችሁ ተመለሱ፡፡ ብርሃንንም ፈልጉ» ይባላሉ፡፡ ግቢው በውስጡ ችሮታ (ገነት) ያለበት ውጭውም ከበኩሉ ስቃይ (እሳት) ያለበት የኾነ (ደጃፍ ባለው አጥር)፡፡

«ከእናንተ ጋር አልነበርንምን?» በማለት ይጠሩዋቸዋል፡፡ «እውነት ነው፡፡ ግን እናንተ ነፍሶቻችሁን አጠፋችሁ፡፡ (በነቢዩ አደጋዎችን) ተጠባበቃችሁም፡፡ ተጠራጠራችሁም፡፡ የአላህም ትዕዛዝ እስከ መጣ ድረስ ከንቱ ምኞቶች አታለሏችሁ፡፡ አታላዩም (ሰይጣን) በአላህ (መታገስ) ሸነገላችሁ፤» ይሏቸዋል፡፡

«ዛሬም ከእናንተ ቤዛ አይወስድም፡፡ ከእነዚያ ከካዱትም፡፡ መኖሪያችሁ እሳት ናት፡፡ እርሷ ተገቢያችሁ ናት፡፡ ምን ትከፋም መመለሻ!» (ይሏቸዋል)፡፡

ለነዚያ ለአመኑት ለአላህ ተግሳጽና ከቁርኣንም ለወረደው ልቦቻቸው ሊፈሩ እንደእነዚያም በፊት መጽሐፍን እንደ ተሰጡትና በእነርሱ ላይ ጊዜ እንደረዘመባቸው ልቦቻቸውም እንደ ደረቁት ላይኾኑ (ጊዜው) አልቀረበምን? ከእነርሱም ብዙዎቹ አመጸኞች ናቸው፡፡

አላህ ምድርን ከሞተች በኋላ ሕያው የሚያደርጋት መኾኑን ዕወቁ፡፡ ታወቁ ዘንድ አንቀጾችን ለእናንተ በእርግጥ አብራራንላችሁ፡፡

የመጸወቱ ወንዶችና፣ የመጸወቱ ሴቶች፣ ለአላህም መልካምን ብድር ያበደሩ ለእነርሱ መልካም ምንዳ አልላቸው፡፡

እነዚያም በአላህና በመልክተኞቹ ያመኑት እነዚያ እነርሱ በጣም እውነተኞቹ በጌታቸውም ዘንድ መስካሪዎቹ ናቸው፡፡ ለእነርሱ ምንዳቸው ብርሃናቸውም አልላቸው፡፡ እነዚያም የካዱት በአንቀጾቻችንም ያስተባበሉት እነዚያ የእሳት ጓዶች ናቸው፡፡

ቅርቢቱ ሕይወት ጨዋታና ዛዛታ፣ ማጌጫም፣ በመካከላችሁም መፎካከሪያ፣ በገንዘቦችና በልጆችም ብዛት መበላለጫ ብቻ መኾንዋን ዕወቁ፡፡ (እርሷ) በቃዩ ገበሬዎችን እንደሚያስደስት ዝናም፣ ከዚያም በቃዩ እንደሚደርቅና ገርጥቶ እንደምታየው፣ ከዚያም የተሰባበረ እንደሚኾን ብጤ ናት፣ በመጨረሻይቱም ዓለም ብርቱ ቅጣት ከአላህም ምሕረትና ውዴታ አልለ፡፡ የቅርቢቱም ሕይወት የመታለያ ጥቅም እንጅ ሌላ አይደለችም፡፡

ከጌታችሁ ወደ ኾነች ምሕረት፣ ወርዷ እደ ሰማይና ምድር ወርድ ወደ ሆነችም ገነት ተሽቀዳደሙ፡፡ ለእነዚያ በአላህና በመልክተኞቹ ላመኑት ተዘጋጅታለች፡፡ ይህ የአላህ ችሮታ ነው፡፡ ለሚሻው ሰው ይሰጠዋል፡፡ አላህም የታላቅ ችሮታ ባለቤት ነው፡፡

በምድርም በነፍሶቻችሁም መከራ (ማንንም) አትነካም ሳንፈጥራት በፊት በመጽሐፍ የተመዘገበች ብትኾን እንጅ፡፡ ይህ በአላህ ላይ ገር ነው፡፡

(ይህ ማሳወቃችን) ባመለጣችሁ ጸጋ ላይ እንዳታዝኑ አላህም በሰጣችሁ ነገር (በትዕቢት) እንዳትደሰቱ ነው፡፡ አላህም ኩራተኛን ጉረኛን ሁሉ አይወድም፡፡

(እነርሱም) እነዚያ የሚሰስቱና ሰዎችንም በስስት የሚያዝዙ ናቸው፡፡ (ከእውነት) የሚሸሽም ሰው (ጥፋቱ በራሱ ላይ ነው)፡፡ አላህም እርሱ ተብቃቂ ምስጉን ነው፡፡

መልክተኞቻችንን በግልጽ ማስረጃዎች በእርግጥ ላክን፡፡ ሰዎችም በትክክል ቀጥ እንዲሉ መጽሐፎችንና ሚዛንን ወደእነርሱ አወረድን፤ ብረትንም በውስጡ ብርቱ ኀይልና ለሰዎችም መጠቃቀሚያዎች ያልሉበት ሲኾን አወረድን፡፡ (እንዲጠቀሙበት) አላህም ሃይማኖቱንና መልክተኞቹን በሩቅ ኾኖ የሚረዳውን ሰው ሊያውቅ (ሊገልጽ አወረደው)፡፡ አላህ ብርቱ አሸናፊ ነውና፡፡

ኑሕን፣ ኢብራሂምንም በእርግጥ ላክን፡፡ በዘሮቻቸውም ውስጥ ነቢይነትንና መጽሐፎችን አደረግን፡፡ ከእነርሱም ቅን አልለ፡፡ ከእነርሱም ብዙዎቹ አመጸኞች ናቸው፡፡

ከዚያም በዱካዎቻቸው ላይ መልክተኞቻችንን አስከታተልን፡፡ የመርየምን ልጅ ዒሳንም አስከተልን፡፡ ኢንጂልንም ሰጠነው፡፡ በእነዚያም በተከተሉት (ሰዎች) ልቦች ውሰጥ መለዘብንና እዝነትን፣ አዲስ የፈጠሩዋትንም ምንኩስና አደረግን፡፡ በእነርሱ ላይ (ምንኩስናን) አልጻፍናትም፡፡ ግን የአላህን ውዴታ ለመፈለግ ሲሉ (ፈጠሩዋት)፡፡ ተገቢ አጠባበቋንም፤ አልጠበቋትም፡፡ ከእነርሱም ለእነዚያ ላመኑት ምንዳቸውን ሰጠናቸው፡፡ ከእነርሱም ብዙዎቹ አመጸኞች ናቸው፡፡

እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አላህን ፍሩ፡፡ በመልእክተኛውም እመኑ፡፡ ከችሮታው ሁለትን ክፍሎች ይሰጣችኋልና፡፡ ለእናንተም በእርሱ የምትኼዱበት የኾነ ብርሃንን ያደርግላችኋል፡፡ ለእናንተም ይምራል፡፡ አላህም መሓሪ አዛኝ ነው፡፡

(ይህም) የመጽሐፉ ሰዎች ከአላህ ችሮታ በምንም ላይ የማይችሉ መኾናቸውን ችሮታም በአላህ እጅ ነው፡፡ ለሚሻው ሰው ይሰጠዋል ማለትን እንዲያውቁ ነው፤ አላህም የታላቅ ችሮታ ባለቤት ነው፡፡
Icon