ترجمة سورة إبراهيم

Sadiq and Sani - Amharic translation
ترجمة معاني سورة إبراهيم باللغة الأمهرية من كتاب Sadiq and Sani - Amharic translation .


አ.ለ.ረ (አሊፍ ላም ራ፤ ይህ ቁርአን) ሰዎችን በጌታቸው ፈቃድ ከጨለማዎች ወደ ብርሃን አሸናፊ ምስጉን ወደ ኾነው፡፡ ጌታ መንገድ ታወጣ ዘንድ ወዳንተ ያወረድነው መጽሐፍ ነው፡፡

አላህ ያ በሰማያት ያለው በምድርም ያለው ሁሉ የርሱ ብቻ የኾነ ነው፤ ለከሓዲዎችም ከብርቱ ቅጣት ወዮላቸው፡፡

እነዚያ የቅርቢቱን ሕይወት ከመጨረሻይቱ ሕይወት ይበልጥ የሚወዱ ከአላህም መንገድ የሚያግዱ መጥመሟንም የሚፈልጉዋት ናቸው፡፡ እነዚያ በሩቅ ስሕተት ውስጥ ናቸው፡፡

ከመልክተኛ ማንኛውንም ለእነርሱ ያብራራላቸው ዘንድ በወገኖቹ ቋንቋ እንጂ በሌላ አልላክንም፡፡ አላህም የሚሻውን ያጠማል፡፡ የሚሻውንም ያቀናል፡፡ እርሱም አሸናፊው ጥበበኛው ነው፡፡

ሙሳንም ወገኖችህን ከጨለማዎች ወደ ብርሃን አውጣ አላህንም ቀኖች አስገንዝባቸው በማለት በተዓምራታችን በእርግጥ ላክነው፡፡ በዚህ ውስጥ በብዙ ታጋሽና በብዙ አመስጋኝ ለኾኑት ሁሉ በእርግጥ ተዓምራቶች አሉ፡፡

ሙሳም ለሕዝቦቹ ባለ ጊዜ (አስታውስ)፤ ከፈርዖን ቤተሰቦች መጥፎን ቅጣት የሚያቀምሱዋችሁ ወንዶች ልጆቻችሁንም የሚያርዱ ሴቶቻችሁንም የሚተዉ ሲኾኑ በአዳንናችሁ ጊዜ በእናንተ ላይ (የዋለላችሁን) የአላህን ጸጋ አስታውሱ፡፡ በዚህም ከጌታችሁ የኾነ ታላቅ ፈተና አለበት፡፡

ጌታችሁም «ብታመሰግኑ በእርግጥ እጨምርላችኋለሁ ብትክዱም (እቀጣችኋለሁ) ቅጣቴ በእርግጥ ብርቱ ነውና» በማለት ባስታወቀ ጊዜ (አስታውሱ)፡፡

ሙሳም አለ «እናንተም በምድር ያለውም ሁሉ በመላ ብትክዱ አላህ በእርግጥ ተብቃቂ ምስጉን ነው፡፡»

የእነዚያ ከናንተ በፊት የነበሩት የኑሕ ሕዝቦች የዓድም የሰሙድም የእነዚያም ከእነሱ በኋለ የነበሩት ከአላህ በስተቀር ሌላ የማያውቃቸው (ሕዝቦች) ወሬ አልመጣላችሁምን መልክተኞቻቸው በማስረጃዎች መጧቸው፡፡ እጆቻቸውንም (በቁጭት ሊነክሱ) ወደ አፎቻቸው መለሱ፡፡ አሉም «እኛ እናንተ በርሱ በተላካችሁበት ነገር ካድን እኛም ወደርሱ ከምትጠሩን ነገር አወላዋይ በኾነ ጥርጣሬ ውስጥ ነን፡፡»

መልክተኞቻቸው «ከኀጢአቶቻችሁ እንዲምራችሁ ወደ ተወሰነ ጊዜም (ያለ ቅጣት) እንዲያቆያችሁ የሚጠራችሁ ሲኾን ሰማያትንና ምድርን ፈጣሪ በኾነው አላህ (በመኖሩ) ጥርጣሬ አለን» አሏቸው፡፡ (ሕዝቦቹም) «እናንተ ብጤያችን ሰው እንጂ አይደላችሁም አባቶቻችን ይገዙት ከነበሩት ልትከለክሉን ትሻላችሁ፡፡ ግልጽንም አስረጅ (ካመጣችሁት ሌላ) አምጡልን» አሉ፡፡

መልክተኞቻቸው ለእነርሱ አሉ «እኛ ብጤያችሁ ሰው እንጂ ሌላ አይደለንም ግን አላህ ከባሮቹ በሚሻው ሰው ላይ ይለግሳል፡፡ ለእኛም በአላህ ፈቃድ እንጂ ማስረጃን ልናመጣላችሁ አይገባንም፡፡ በአላህም ላይ ምእምናኖች ይጠጉ፡፡

«መንገዳችንንም በእርግጥ የመራን ሲኾን በአላህ ላይ የማንመካ ለእኛ ምን አለን በማሰቃየታችሁም ላይ በእርግጥ እንታገሳለን፡፡ በአላህም ላይ ተመኪዎች ሁሉ ይመኩ፡፡»

እነዚያም የካዱት ለመልክተኞቻቸው «ከምድራችን በእርግጥ እናወጣችኋለን፤ ወይም ወደ ሃይማኖታችን በእርግጥ ትመለሳላችሁ» አሉ፡፡ ወደእነርሱም ጌታቸው እንዲህ ሲል ላከ «ከሓዲዎችን በእርግጥ እናጠፋለን፡፡

«ከእነሱም በኋላ ምድሪቱን በእርግጥ እናስቀምጣችኋለን፡፡ ይኸ በፊቴ መቆሙን ለሚፈራ ዛቻዬንም ለሚፈራ ሰው ነው፡፡»

እርዳታንም (ከአላህ) ፈለጉ፤ (ተረዱም)፡፡ ጨካኝ ሞገደኛ የኾነም ሁሉ አፈረ፡፡

ከስተፊቱ ገሀነም አለበት፡፡ እዥ ከኾነም ውሃ ይጋታል፡፡

ይጎነጨዋል፤ ሊውጠውም አይቀርብም፡፡ ሞትም ከየስፍራው ሁሉ ይመጣበታል፤ እርሱም የሚሞት አይደለም፡፡ ከስተፊቱም ከባድ ቅጣት አለ፡፡

የእነዚያ በጌታቸው የካዱት ሰዎች ምሳሌ (መልካም) ሥራዎቻቸው በነፋሻ ቀን ነፋስ በርሱ እንደ በረታችበት አመድ ነው፡፡ በሠሩት ሥራ በምንም ላይ (ሊጠቀሙ) አይችሉም፡፡ ይህ እርሱ ሩቅ ጥፋት ነው፡፡

አላህ ሰማያትንና ምድርን በእውነት የፈጠረ መኾኑን አታይምን ቢሻ ያጠፋችኋል፡፡ አዲስ ፍጡርንም ያመጣል፡፡

ይህም በአላህ ላይ አስቸጋሪ አይደለም፡፡

የተሰበሰቡም ኾነው ለአላህ ይገለጻሉ፡፡ (ሐሳበ) ደካማዎቹም (ተከታዮች) ለእነዚያ ለኮሩት «እኛ ለእናንተ ተከታዮች ነበርን፤ እናንተ ከአላህ ቅጣት ከኛ ላይ አንዳችን ነገር ተከላካዮች ናችሁን» ይላሉ፡፡ (አስከታዮቹም) «አላህ ባቀናን ኖሮ በእርግጥ በመራናችሁ ነበር» ይሏቸዋል፡፡ «ብንበሳጭ ወይም ብንታገስም በእኛ ላይ እኩል ነው፡፡ ለእኛ ምንም መጠጊያ የለንም» ይላሉ፡፡

ነገሩም በተፈጸመ ጊዜ ሰይጣን ይላቸዋል «አላህ እውነተኛውን ቃል ኪዳን ገባላችሁ፡፡ ቃል ኪዳንም ገባሁላችሁ፤ አፈረስኩባችሁም፡፡ ለእኔም በእናንተ ላይ ምንም ስልጣን አልበረኝም፡፡ ግን ጠራኋችሁ፡፡ ለእኔም ታዘዛችሁ፡፡ ስለዚህ አትውቀሱኝ፤ ነፍሶቻችሁንም ውቀሱ፡፡ እኔ የምረዳችሁ አይደለሁም፡፡ እናንተም የምትረዱኝ አይደላችሁም፡፡ እኔ ከአሁን በፊት ለአላህ ተጋሪ በአደረጋችሁት ነገር ካድኩ፡፡ በዳዮቹ ለእነርሱ በእርግጥ አሳማሚ ቅጣት አላቸው፡፡»

እነዚያም ያመኑና መልካም ሥራዎችን የሠሩ ከሥሮቻቸው ወንዞች የሚፈሱባቸውን ገነቶች በውስጣቸው ዘውታሪዎች ሲኾኑ በጌታቸው ፈቃድ እንዲገቡ ይደረጋሉ፡፡ በውስጣቸው መከባበሪያቸው ሰላም (ለእናንተ ይኹን መባባል) ነው፡፡

አላህ መልካምን ቃል ሥርዋ (በምድር ውስጥ) የተደላደለች ቅርንጫፍዋም ወደ ሰማይ (የረዘመች) እንደሆነች መልካም ዛፍ አድርጎ ምሳሌን እንዴት እንደገለጸ አላየኽምን

ምግቧን (ፍሬዋን) በጌታዋ ፈቃድ በየጊዜው ትሰጣለች፡፡ አላህም ለሰዎች ይገሰጹ ዘንድ ምሳሌዎችን ይገልጻል፡፡

የመጥፎም ቃል ምሳሌ ከምድር በላይ የተጎለሰሰች ለእርሷ ምንም መደላደል የሌላት እንደኾነች መጥፎ ዛፍ ነው፡፡

አላህ እነዚያን ያመኑትን በቅርቢቱም ሕይወት በመጨረሻይቱም (በመቃብር) በተረጋገጠው ቃል ላይ ያረጋቸዋል፡፡ ከሓዲዎችንም አላህ ያሳስታቸዋል፡፡ አላህም የሚሻውን ይሠራል፡፡

ወደእነዚያ የአላህን ጸጋ በክህደት ወደ ለወጡት ሕዝቦቻቸውንም በጥፋት አገር ወዳሰፈሩት (ወደ ቁረይሾች) አላየህምን

(አገሪቱም) የሚገቧት ስትኾን ገሀነም ናት፡፡ ምን ትከፋም መርጊያ!

ለአላህም ከመንገዱ ያሳስቱ ዘንድ ባላንጣዎችን አደረጉለት፡፡ «(ጥቂትን) ተጠቀሙ መመለሻችሁም ወደ እሳት ነው» በላቸው፡፡

ለእነዚያ ላመኑት ባሮቼ በእርሱ ውስጥ ሽያጭና ወዳጂነት የሌለበት ቀን ከመምጣቱ በፊት ሶላትን በደንቡ ይሰግዳሉ፡፡ ከሰጠናቸውም ሲሳይ በምስጢርም በግልጽም ይለግሳሉ፡፡ (ስገዱ ለግሱም) በላቸው፡፡

አላህ ያ ሰማያትንና ምድርን የፈጠረ ከሰማይም ውሃን ያወረደ በእርሱም ከፍሬዎች ሲሳይን ለእናንተ ያወጣ መርከቦችንም በፈቃዱ በባሕር ላይ ይንሻለሉ ዘንድ ለናንተ የገራ ወንዞችንም ለናንተ የገራ ነው፡፡

ፀሐይንና ጨረቃንም ዘወትር ኼያጆች ሲኾኑ ለእናንተ የገራ ሌሊትንና ቀንንም ለእናንተ የገራላችሁ ነው፡፡

ከለመናችሁትም ሁሉ የሰጣችሁ ነው፡፡ የአላህንም ጻጋ ብትቆጥሩ አትዘልቋትም፡፡ ሰው በጣም በደለኛ ከሓዲ ነው፡፡

ኢብራሂምም ባለ ጊዜ (አስታውስ) «ጌታዬ ሆይ! ይህንን አገር (መካን) ጸጥተኛ አድርገው፡፡ እኔንም ልጆቼንም ጣዖታትን ከመገዛት አርቀን፡፡

«ጌታዬ ሆይ! እነርሱ (ጣዖታት) ከሰዎች ብዙዎችን አሳስተዋልና፡፡ የተከተለኝም ሰው እርሱ ከኔ ነው፡፡ ትእዛዜንም የጣሰ ሰው አንተ መሓሪ አዛኝ ነህ፡፡

«ጌታችን ሆይ! እኔ አዝመራ በሌለው ሸለቆ ውስጥ በተከበረው ቤት (በካዕባ) አጠገብ ከዘሮቼ አስቀመጥኩ፡፡ ጌታችን ሆይ! ሶላትን ያቋቁሙ ዘንድ (አስቀመጥኳቸው)፡፡ ከሰዎችም ልቦችን ወደእነሱ የሚናፍቁ አድርግ፡፡ ያመሰግኑህም ዘንድ ከፍሬዎች ስጣቸው፡፡

«ጌታችን ሆይ! አንተ የምንደብቀውንም የምንገልጸውንም ሁሉ በእርግጥ ታውቃለህ፡፡ በአላህም ላይ በምድርም በሰማይም ምንም ነገር አይደበቅም፡፡

«ለእዚያ ከሽምግልና በኋላ ኢስማዒልን ኢስሐቅንም ለእኔ ለሰጠኝ አላህ ምሰጋና ይገባው፡፡ ጌታዬ ልመናን በእርግጥ ሰሚ ነውና፡፡

«ጌታዬ ሆይ! ሰላትን አዘውትሬ የምሰግድ አድርገኝ፡፡ ከዘሮቼም (አድርግ)፡፡ ጌታችን ሆይ! ጸሎቴንም ተቀበለኝ፤

«ጌታችን ሆይ! ለእኔም ለወላቼም ለምእመናንም ሁሉ ምርመራ በሚደረግበት ቀን ማር፡፡»

አላህንም በደለኞች ከሚሠሩት ግፍ ዘንጊ አድርገህ አታስብ፡፡ የሚያቆያቸው ዓይኖች በእርሱ እስከሚፈጡበት ቀን ድረስ ብቻ ነው፡፡

(ወደ ጠሪው መልአክ) ቸኳዮች ራሶቻቸውን አንጋጣጮች ኾነው (ዓይኖቻቸው ይፈጣሉ)፡፡ ዓይኖቻቸው ወደነርሱ አይመለሱም፡፡ ልቦቻቸውም ባዶዎች ናቸው፡፡

ሰዎችንም ቅጣቱ የሚመጣባቸውን ቀን አስፈራራቸው፡፡ እነዚያም የበደሉት «ጌታችን ሆይ! ወደ ቅርበ ጊዜ ድረስ አቆየን፡፡ ጥሪህን እንቀበላለንና መልክተኞቹንም እንከተላለንና» ይላሉ፡፡ «ከአሁን በፊት (በምድረ ዓለም) ለእናንተ ምንም መወገድ የላችሁም በማለት የማላችሁ አልነበራችሁምን» (ይባላሉ)፡፡

«በእነዚያም ነፍሶቻቸውን በበደሉት ሰዎች መኖሪያ ውስጥ ተቀመጣችሁ፡፡ በእነሱም እንዴት እንደሠራንባቸው ለእናንተ ተገለጸላችሁ፡፡ ለእናንተም ምሳሌዎችን ገለጽንላችሁ፡፡»

(በነቢዩ ላይ) ሴራቸውንም በእርግጥ አሴሩ፡፡ ሴራቸውም (ቅጣቱ) አላህ ዘንድ ነው፡፡ ሴራቸውም ኮረብታዎች (ሕግጋቶች) በእርሱ የሚወገዱበት አልነበረም፡፡

አላህንም መልክተኞቹን (የገባላቸውን) ቃል ኪዳኑን አፍራሽ አድርገህ አታስብ፡፡ አላህ አሸናፊ የመበቀል ባለቤት ነው፡፡

ምድር በሌላ ምድር የምትለወጥበትን ሰማያትም (እንደዚሁ) አንድ አሸናፊ ለኾነው አላህም (ፍጡራን ሁሉ) የሚገለጹበት ቀን (አስታውሱ)፡፡

አመጸኞችንም በዚያ ቀን በሰንሰለቶች ተቆራኝተው ታያቸዋለህ፡፡

ቀሚሶቻቸው ከካትራም ናቸው፡፡ ፊቶቻቸውንም እሳት ትሸፍናቸዋለች፡፡

አላህ ነፍስን ሁሉ የሠራችውን ይመነዳ ዘንድ (ይህንን አደረገ)፡፡ አላህ ምርመራው ፈጣን ነው፡፡

ይህ (ቁርኣን) ለሰዎች ገላጭ ነው፡፡ (ሊመከሩበት)፣ በእርሱም ሊስፈራሩበት፣ እርሱም አንድ አምላክ ብቻ መኾኑን ሊያውቁበት፣ የአእምሮ ባለቤቶችም ሊገሰፁበት (የተወረደ) ነው፡፡
Icon