የሱራ النساء ትርጉም በالأمهرية ከSadiq and Sani - Amharic translation
Verse 1
እናንተ ሰዎች ሆይ! ያንን ከአንዲት ነፍስ (ከአዳም) የፈጠራችሁን ከእርስዋም መቀናጆዋን (ሔዋንን) የፈጠረውን ከእነርሱም ብዙ ወንዶችንና ሴቶች የበተነውን ጌታችሁን ፍሩ፡፡ ያንንም በርሱ የምትጠያየቁበትን አላህንና ዝምድናዎችንም (ከመቁረጥ) ተጠንቀቁ፡፡ አላህ በእናንተ ላይ ተጠባባቂ ነውና፡፡
Verse 2
የቲሞችንም ገንዘቦቻቸውን ስጡ፡፡ መጥፎውንም በመልካሙ አትለውጡ፡፡ ገንዘቦቻቸውንም ወደ ገንዘቦቻችሁ (በመቀላቀል) አትብሉ እርሱ ታላቅ ኃጢአት ነውና፡፡
Verse 3
በየቲሞችም (ማግባት) አለማስተካከላችሁን ብትፈሩ (ዝሙትንና ከተወሰነላችሁ በላይ ማግባትንም ፍሩ)፡፡ ከሴቶች ለእናንተ የተዋበላችሁን ሁለት ሁለት ሦስት ሦስትም አራት አራትም አግቡ፡፡ አለማስተካከልንም ብትፈሩ አንዲትን ብቻ ወይም እጆቻችሁ ንብረት ያደረጉትን ያዙ፡፡ ይህ ወደ አለመበደል በጣም የቀረበ ነው፡፡
Verse 4
ሴቶችንም መህሮቻቸውን በደስታ ስጡ፡፡ ለእናንተም ከእርሱ አንዳችን ነገር ነፍሶቻቸው ቢለግሱ መልካም ምስጉን ሲኾን ብሉት፡፡
Verse 5
ቂሎችንም ያችን አላህ ለእናንተ መተዳደሪያ ያደረጋትን ገንዘቦቻችውን (የያዛችሁላቸውን) አትስጡዋቸው፡፡ ከርሷም መግቡዋቸው አልብሱዋቸውም፡፡ ለእነሱም መልካምን ንግግር ተናገሩ፡፡
የቲሞችንም ጋብቻን እስከደረሱ ጊዜ ድረስ ፈትኑዋቸው፡፡ ከእነርሱም ቅንነትን ብታውቁ ገንዘቦቻቸውን ወደ እነርሱ ስጡ፡፡ በማባከንና ማደጋቸውንም በመሽቀዳደም አትብሏት፡፡ (ከዋቢዎች) ሀብታምም የኾነ ሰው ይከልከል፡፡ ድሃም የኾነ ሰው (ለድካሙ) በአግባብ ይብላ፡፡ ገንዘቦቻቸውንም ወደ እነርሱ በሰጣችሁ ጊዜ በእነርሱ ላይ አስመስክሩ፡፡ ተጠባባቂነትም በአላህ በቃ፡፡
Verse 7
ለወንዶች ወላጆችና የቅርብ ዘመዶች ከተዉት (ንብረት) ፋንታ (ድርሻ) አላቸው፡፡ ለሴቶችም ወላጆችና የቅርብ ዘመዶች ከተዉት ከእርሱ ካነሰው ወይም ከበዛው ፋንታ አላቸው፡፡ የተወሰነ ድርሻ (ተደርጓል)፡፡
Verse 8
ክፍያንም (ወራሽ ያልኾኑ) የዝምድና ባለቤቶችና የቲሞች፣ ምስኪኖችም በተገኙበት ጊዜ ከእርሱ ዳርጓቸው፡፡ መልካምንም ንግግር ተናገሩዋቸው፡፡
Verse 9
እነዚያም ከኋላቸው ደካሞችን ዝርያዎች ቢተው ኖሮ በእነርሱ ላይ የሚፈሩ (በየቲሞች ላይ) ይጠንቀቁ፡፡ አላህንም ይፍሩ፡፡ (ለተናዛዡ) ትክክለኛንም ቃል ይናገሩ፡፡
Verse 10
እነዚያ የየቲሞችን ገንዘብ በመበደል የሚበሉ በሆዶቻቸው ውስጥ የሚበሉት እሳትን ብቻ ነው፡፡ እሳትንም በእርግጥ ይገባሉ፡፡
አላህ በልጆቻችሁ (ውርስ በሚከተለው) ያዛችኋል፡፡ ለወንዱ የሁለት ሴቶች ድርሻ ብጤ አለው፡፡ (ሁለት ወይም) ከሁለት በላይም የኾኑ ሴቶች ብቻ ቢኾኑ ለእነሱ (ሟቹ) ከተወው ረጀት (ድርሻ) ከሦስት ሁለት እጁ አላቸው፡፡ አንዲትም ብትኾን ለርሷ ግማሹ አላት፡፡ ለአባትና ለእናቱም ለእርሱ ልጅ እንዳለው ከሁለቱ ለያንዳንዱ ከስድስት አንድ አላቸው፡፡ ለእርሱም ልጅ ባይኖረውና ወላጆቹ ቢወርሱት ለእናቱ ሲሶው አላት፡፡ ለእርሱም ወንድሞችና እኅቶች ቢኖሩት ለናቱ ከስድስት አንድ አላት፡፡ (ይህም የተባለው) በርሷ ከተናዘዘባት ኑዛዜ ወይም ከዕዳ በኋላ ነው፡፡ አባቶቻችሁና ልጆቻችሁ ለእናንተ በመጥቀም ማንኛቸው ይበልጥ ቅርብ እንደኾኑ አታውቁም፡፡ (ይኽም) ከአላህ የተደነገገ ነው፤ አላህ ዐዋቂ ጥበበኛ ነውና፡፡
ለእናንተም ሚስቶቻችሁ ከተዉት ንብረት ለእነርሱ ልጅ ባይኖራቸው ግማሹ አላችሁ፡፡ ለእነሱም ልጅ ቢኖራቸው ከተዉት ሀብት ከአራት አንድ አላችሁ፡፡ (ይህም) በእርሷ ከሚናዘዙባት ኑዛዜ ወይም ከዕዳ በኋላ ነው፡፡ ለናንተም ልጅ ባይኖራችሁ ከተዋችሁት ንብረት ለእነርሱ (ለሚስቶች) ከአራት አንድ አላቸው፡፡ ለእናንተም ልጅ ቢኖራችሁ ከተዋችሁት ንብረት ለእነርሱ ከስምንት አንድ አላቸው (ይህም በርሷ ከምትናዘዙባት ኑዛዜ ወይም ከዕዳ በኋላ ነው፡፡) ወላጅም ልጅም የሌለው በጎን ወራሾች የሚወርስ ወንድ ወይም ሴት ቢገኝ ለእርሱም (ለሟቹ) ወንድም ወይም እኅት (ከእናቱ በኩል ብቻ የኾነ) ቢኖር ከሁለቱ ለያንዳንዳቸው ከስድስት አንድ አላቸው፡፡ ከዚህም (ከአንድ) የበዙ ቢኾኑ እነርሱ በሲሶው ተጋሪዎች ናቸው፡፡ (ይህም ወራሾችን) የማይጎዳ ኾኖ በእርሷ ከሚናዘዙባት ኑዛዜ ወይም ከዕዳ በኋላ ነው፡፡ ከአላህም የኾነን ኑዛዜ (ያዛችኋል)፡፡ አላህም ዐዋቂ ቻይ ነው፡፡
Verse 13
እነዚህ የአላህ ውሳኔዎች ናቸው፡፡ አላህንና መልክተኛውንም የሚታዘዙ ሰዎች ከሥሮቻቸው ወንዞች የሚፈሱባቸውን ገነቶች በውስጣቸው ዘውታሪዎች ሲኾኑ ያገባቸዋል፡፡ ይህም ትልቅ ዕድል ነው፡፡
Verse 14
አላህንና መልክተኛውንም የሚያምጽ ወሰኖቹንም የሚተላለፍ በውስጧ ዘውታሪ ሲኾን እሳትን ያገባዋል፡፡ ለርሱም አዋራጅ ቅጣት አለው፡፡
Verse 15
እነዚያም ከሴቶቻችሁ መጥፎን ሥራ (ዝሙትን) የሚሠሩ በእነርሱ ላይ ከናንተ አራትን (ወንዶች) አስመስክሩባቸው፡፡ ቢመሰክሩም ሞት እስከሚደርስባቸው ወይም አላህ ለእነርሱ መንገድን እስከሚያደርግ ድረስ በቤቶች ውሰጥ ያዙዋቸው (ጠብቁዋቸው)፡፡
Verse 16
እነዚያንም ከእናንተ ውስጥ (ዝሙትን) የሚሠሩዋትን አሰቃዩዋቸው፡፡ ቢጸጸቱና ሥራቸውንም ቢያሳምሩ ከእነርሱ ተገቱ (አታሰቃዩዋቸው)፡፡ አላህ ጸጸትን ተቀባይ አዛኝ ነውና፡፡
Verse 17
ጸጸትን መቀበል በአላህ ላይ የሚገባው ለእነዚያ ኀጢአትን በስህተት ለሚሠሩና ከዚያም ከቅርብ ጊዜ ለሚጸጸቱት ብቻ ነው፡፡ እነዚያንም አላህ በእነርሱ ላይ ጸጸትን ይቀበላል፡፡ አላህም ዐዋቂ ጥበበኛ ነው፡፡
Verse 18
ጸጸትንም መቀበል ለእነዚያ ኀጢአቶችን ለሚሠሩ አንዳቸውንም ሞት በመጣበት ጊዜ «እኔ አሁን ተጸጸትኩ» ለሚልና ለነዚያም እነርሱ ከሓዲዎች ኾነው ለሚሞቱ አይደለችም፡፡ እነዚያ ለእነሱ አሳማሚን ቅጣት አዘጋጅተናል፡፡
Verse 19
እናንተ ያመናችሁ ሰዎች ሆይ! ሴቶችን ያስገደዳችሁ ኾናችሁ ልትወርሱና ግልጽን መጥፎ ሥራ ካልሠሩ በስተቀር ከሰጣችኋቸው ከፊሉን ልትወስዱ ልታጉላሏቸውም ለእናንተ አይፈቀድም፡፡ በመልካምም ተኗኗሩዋቸው፡፡ ብትጠሉዋቸውም (ታገሱ)፡፡ አንዳችን ነገር ብትጠሉ አላህም በእርሱ ብዙ ደግ ነገርን ሊያደርግ ይቻላልና፡፡
Verse 20
በሚስትም ስፍራ ሚስትን ለመለወጥ ብትፈልጉ ለአንደኛይቱ (ለምትፈታው) ብዙን ገንዘብ የሰጣችኋት ስትኾኑ ከርሱ ምንንም አትውሰዱ፡፡ በመበደልና ግልጽ በኾነ ኀጢአት ትወስዱታላችሁን
Verse 21
ከፊላችሁ ወደ ከፊሉ በእርግጥ የደረሰ ሲኾንና ከእናንተ ላይም (ሴቶች) የጠበቀ ኪዳንን የያዙባችሁ ሲኾኑ እንዴት ትወስዱታላችሁ!
Verse 22
ከሴቶችም አባቶቻችሁ ያገቡዋቸውን አታግቡ፡፡ (ትቀጡበታላችሁ)፡፡ ያለፈው ሲቀር፡፡ እርሱ መጥፎና የተጠላ ሥራ ነውና፡፡ መንገድነቱም ከፋ!
እናቶቻችሁ፣ ሴት ልጆቻችሁም፣ እኅቶቻችሁም፣ አክስቶቻችሁም፣ የሹሜዎቻችሁም፣ የወንድም ሴቶች ልጆችም፣ የእኅት ሴቶች ልጆችም፣ እነዚያም ያጠቡዋችሁ እናቶቻችሁ፣ ከመጥባት የኾኑትም እኅቶቻችሁ፣ የሚስቶቻችሁም እናቶች፣ እነዚያም በጉያዎቻችሁ ያሉት የእነዚያ በእነርሱ የገባችሁባቸው ሚስቶቻችሁ ሴቶች ልጆች፣ (ልታገቧቸው) በእናንተ ላይ እርም ተደረጉባችሁ፡፡ በእነርሱም (በሚስቶቻችሁ) ያልገባችሁባቸው ብትኾኑ (በፈታችኋቸው ጊዜ ሴቶች ልጆቻቸውን ብታገቡ) በእናንተ ላይ ኀጢአት የለባችሁም፡፡ የእነዚያ ከጀርባዎቻችሁ የኾኑት ወንዶች ልጆቻችሁ ሚስቶችም በሁለት እኅትማማቾችም መካከል መሰብሰብ (እንደዚሁ እርም ነው)፡፡ ግን ከዚህ በፊት ያለፈው ሲቀር (እርሱንስ ተምራችኋል) አላህ መሓሪ አዛኝ ነውና፡፡
ከሴቶችም (በባል) ጥብቆቹ እጆቻቸሁ (በምርኮ) የያዙዋቸው ሲቀሩ በእናንተ ላይ እርም ናቸው፡፡ (ይህን) አላህ በናንተ ላይ ጻፈ፡፡ ከዚሃችሁም (ከተከለከሉት) ወዲያ ጥብቆች ኾናችሁ ዝሙተኞች ሳትኾኑ በገንዘቦቻችሁ ልትፈልጉ ለእናንተ ተፈቀደ፡፡ ከእነሱም በርሱ (በመገናኘት) የተጠቀማችሁባቸውን ሴቶች መህሮቻቸውን ግዴታ ሲኾን ስጧቸው፡፡ ከመወሰንም በኋላ በተዋደዳችሁበት ነገር በእናንተ ላይ ኀጢአት የለም፡፡ አላህ ዐዋቂ ጥበበኛ ነውና፡፡
ከናንተም ውስጥ ጥብቆች ምእምናት የኾኑትን ለማግባት ሀብትን ያልቻለ ሰው እጆቻችሁ ንብረት ካደረጓቸው ከምእምናት ወጣቶቻችሁ (ባሪያን ያግባ)፡፡ አላህም እምነታችሁን ዐዋቂ ነው፡፡ ከፊላችሁ ከከፊሉ (የተራባ) ነው፡፡ (ባሮችን) በጌቶቻቸውም ፈቃድ አግቡዋቸው፡፡ መህሮቻቸውንም በመልካም መንገድ ስጧቸው፡፡ ጥብቆች ኾነው ዝሙተኞች ያልኾኑ የስርቆሽ ወዳጆችንም ያልያዙ ሲኾኑ (አግቧቸው)፡፡ በማግባት በተጠበቁም ጊዜ መጥፎን ሥራ ቢሠሩ በእነርሱ ላይ ከቅጣት በነጻዎቹ ላይ ያለው ግማሽ አለባቸው፡፡ ይኸ (ባሪያን ማግባት) ከናንተ ዝሙትን ለፈራ ሰው ነው፡፡
Verse 26
አላህ (የሃይማኖታችሁን ሕግጋት) ሊያብራራላችሁ ከእናንተ በፊትም የነበሩትን ነቢያት ደንቦች ሊመራችሁ በእናንተም ላይ ጸጸትን ሊቀበል ይሻል፡፡ አላህም ዐዋቂ ጥበበኛ ነው፡፡
Verse 27
አላህም በእናንተ ላይ ጸጸትን ሊቀበል ይሻል፡፡ እነዚያም ፍላጎታቸውን የሚከተሉት (ከውነት) ትልቅን መዘንበል እንድትዘነበሉ ይፈልጋሉ፡፡
Verse 28
አላህ ከእናንተ ሊያቃልልላችሁ ይሻል፡፡ ሰውም ደካማ ኾኖ ተፈጠረ፡፡
Verse 29
እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ገንዘቦቻችሁን በመካከላችሁ ያለ አግባብ አትብሉ፡፡ ግን ከእናንተ በመዋደድ የኾነችውን ንግድ (ብሉ)፡፡ ነፍሶቻችሁንም አትግደሉ፡፡ አላህ ለእናንተ አዛኝ ነውና፡፡
Verse 30
ወሰን በማለፍና በመበደልም ይህንን የሠራ ሰው እሳትን እናገባዋለን፡፡ ይኸም በአላህ ላይ ገር ነው፡፡
Verse 31
ከእርሱ ከተከለከላችሁት ታላላቆቹን (ኀጢአቶች) ብትርቁ (ትናንሾቹን) ኀጢአቶቻችሁን ከእናንተ እናብሳለን፡፡ የተከበረንም ስፍራ (ገነትን) እናገባችኋለን፡፡
Verse 32
አላህም ከፊላችሁን በከፊሉ ላይ በእርሱ ያበለጠበትን ጸጋ አትመኙ፡፡ ለወንዶች ከሠሩት ሥራ እድል አላቸው፡፡ ለሴቶችም ከሠሩት ሥራ ዕድል አላቸው፡፡ አላህንም ከችሮታው ለምኑት፡፡ አላህ በነገሩ ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡
Verse 33
ለሁሉም (ለወንዶችና ለሴቶች) ወላጆችና የቅርብ ዘመዶች ከተዉት ሀብት ጠቅላይ ወራሾችን አድርገናል፡፡ እነዚያንም (ለመረዳዳትና ለመዋረስ) በመሐላዎቻችሁ የተዋዋላችኋቸውን ድርሻቸውን (ከስድስት አንድ) ስጧቸው፡፡ አላህ በነገሩ ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡
ወንዶች በሴቶች ላይ ቋሚዎች (አሳዳሪዎች) ናቸው፡፡ አላህ ከፊላቸውን በከፊሉ ላይ በማብለጡና (ወንዶች) ከገንዘቦቻቸው (ለሴቶች) በመስጠታቸው ነው፡፡ መልካሞቹም ሴቶች (ለባሎቻቸው) ታዛዦች አላህ ባስጠበቀው ነገር ሩቅን ጠባቂዎች ናቸው፡፡ እነዚያንም ማመጸቸውን የምትፈሩትን ገስጹዋቸው፡፡ በመኝታዎችም ተለዩዋቸው፡፡ (ሳካ ሳታደርሱ) ምቱዋቸውም፡፡ ቢታዘዟችሁም (ለመጨቆን) በእነርሱ ላይ መንገድን አትፈልጉ፤ አላህ የበላይ ታላቅ ነውና፡፡
Verse 35
(እናንተ ዋቢዎች) የመካከላቸውንም ጭቅጭቅ ብታውቁ ከቤተሰቦቹ ሽማግሌን ከቤተሰቦችዋም ሽማግሌን ላኩ፡፡ ማስታረቅን ቢሹ አላህ በመካከላቸው ያስማማል፡፡ አላህ ግልጽን ዐዋቂ ውስጥንም ዐዋቂ ነውና፡፡
Verse 36
አላህንም ተገዙ፡፡ በእርሱም ምንንም አታጋሩ፡፡ በወላጆችና በቅርብ ዝምድና ባለቤትም፣ በየቲሞችም፣ በምስኪኖችም፣ በቅርብ ጎረቤትም፣ በሩቅ ጎረቤትም፣ በጎን ባልደረባም፣ በመንገደኛም፣ እጆቻችሁም ንብረት ባደረጓቸው (ባሮች)፣ መልካምን (ሥሩ)፤ አላህ ኩራተኛ ጉረኛ የኾነን ሰው አይወድም፡፡
Verse 37
እነዚያ የሚሰስቱ ሰዎችንም በመሰሰት የሚያዙ አላህም ከችሮታው የሰጣቸውን ጸጋ የሚደብቁ (ብርቱን ቅጣት ይቀጥጣሉ)፡፡ ለከሓዲዎችም አዋራጅን ቅጣት አዘጋጅተናል፡፡
Verse 38
እነዚያም ለሰዎች ይውልኝ ሲሉ ገንዘቦቻቸውን የሚሰጡ በአላህና በመጨረሻውም ቀን የማያምኑ (ይቀጥጣሉ)፡፡ ሰይጣንም ለእርሱ ጓደኛው የኾነ ሰው ጓደኛነቱ ከፋ!
Verse 39
በአላህና በመጨረሻውም ቀን ባመኑ አላህ ከሰጣቸውም (ሲሳይ) በለገሱ ኖሮ በነርሱ ላይ ምን (ጉዳት) ነበረ አላህም በነርሱ (ኹነታ) ዐዋቂ ነው፡፡
Verse 40
አላህ የብናኝን ክብደት ያህል አይበድልም፡፡ መልካም ሥራ ብትኾንም ይደራርባታል፡፡ ከእርሱም ዘንድ ታላቅን ምንዳ ይሰጣል፡፡
Verse 41
ከሕዝቦችም ሁሉ መስካሪን ባመጣን ጊዜ አንተንም በእነዚህ ላይ መስካሪ አድርገን በምናመጣህ ጊዜ (የከሓዲዎች ኹኔታ) እንዴት ይኾን
Verse 42
በዚያ ቀን እነዚያ የካዱትና መልክተኛውን ያልታዘዙት በእነሱ ምድር ብትደፋባቸው ይመኛሉ፡፡ ከአላህም ወሬን አይደብቁም፡፡
እናንተ ያመናችሁ ሆይ! እናንተ የሰከራችሁ ኾናችሁ የምትሉትን ነገር እስከምታውቁ የረከሳችሁም ስትኾኑ መንገድን አላፊዎች ካልኾናችሁ በስተቀር (አካላታችሁን) እስከምትታጠቡ ድረስ ስግደትን አትቅረቡ፡፡ በሽተኞች ወይም በጉዞ ላይ ብትኾኑም፥ ወይንም ከእናንተ አንዱ ከዓይነምድር ቢመጣ፥ ወይንም ሴቶችን ብትነካኩና ውሃን ባታገኙ፣ ንጹሕ የኾነን የምድር ገጽ አስቡ፡፡ ፊቶቻችሁንና እጆቻችሁንም (በርሱ) አብሱ፡፡ አላህ ይቅር ባይ መሓሪ ነውና፡፡
Verse 44
ወደነዚያ ከመጽሐፉ (ዕውቀት) ዕድልን ወደ ተሰጡት አላየህምን ጥመትን (በቅንነት) ይገዛሉ፡፡ መንገድንም እንድትሳሳቱ ይፈልጋሉ፡፡
Verse 45
አላህም ጠላቶቻችሁን ዐዋቂ ነው፡፡ ጠባቂነትም በአላህ በቃ፡፡ ረዳትነትም በአላህ በቃ፡፡
Verse 46
ከነዚያ አይሁዳውያን ከኾኑት ሰዎች ንግግሮችን ከስፍራዎቹ የሚያጣምሙ አልሉ፡፡ «ሰማንም አመጽንም የማትሰማም ስትኾን ስማ» ይላሉ፡፡ በምላሶቻቸውም ለማጣመምና ሃይማኖትንም ለመዝለፍ ራዒና ይላሉ፡፡ እነሱም «ሰማን ታዘዝንም ስማም ተመልከተንም» ባሉ ኖሮ ለነሱ መልካምና ትክክለኛ በኾነ ነበር፡፡ ግን በክህደታቸው አላህ ረገማቸው፡፡ ጥቂትንም እንጅ አያምኑም፡፡
Verse 47
እናንተ መጽሐፉን የተሰጣችሁ ሆይ! ፊቶችን ሳናብስና በጀርባዎች ላይ ሳንመልሳቸው ወይም የሰንበትን ባለቤቶች (ያፈረሱትን) እንደረገምን ሳንረግማቸው በፊት ከእናንተ ጋር ያለውን የሚያረጋግጥ ኾኖ ባወረድነው (ቁርኣን) እመኑ፡፡ የአላህም ትዕዛዝ ተፈጻሚ ነው፡፡
Verse 48
አላህ በእርሱ ማጋራትን በፍጹም አይምርም፡፡ ከዚህ ሌላ ያለውንም (ኀጢአት) ለሚሻው ሰው ይምራል፡፡ በአላህም የሚያጋራ ሰው ታላቅን ኀጢአት በእርግጥ ቀጠፈ፡፡
Verse 49
ወደእነዚያ ነፍሶቻቸውን ወደ ሚያጠሩት (የሚያወድሱት) አላየህምን አይደለም፤ አላህ የሚፈልገውን ያጠራል፡፡ የተምር ፍሬ ክር ያህልም አይበደሉም፡፡
Verse 50
በአላህ ላይ ውሸትን እንዴት እንደሚቀጣጥፉ ተመልከት፡፡ ግልጽ ወንጀልም በርሱ (በመቅጠፍ) በቃ፡፡
Verse 51
ወደ እነዚያ ከመጽሐፉ ዕድልን ወደ ተሰጡት አላየኸምን በድግምትና በጣዖት ያምናሉ፡፡ ለእነዚያም ለካዱት፡- እናንተ በመንገድ (በሃይማኖት) ከእነዚያ ካመኑት ይበልጥ የቀናችሁ ናችሁ ይላሉ፡፡
Verse 52
እነዚያ አላህ የረገማቸው ናቸው፡፡ አላህም የረገመው ሰው ለእርሱ ፈጽሞ ረዳትን አታገኝለትም፡፡
Verse 53
በእውነቱ ለእነሱ ከንግሥናው ፋንታ አላቸውን ያን ጊዜ ለሰዎች በተምር ፍሬ ላይ ያለችውን ነጥብ ያህል አይሰጡም ነበር፡፡
Verse 54
ይልቁንም ሰዎችን (ሙሐመድን) አላህ ከችሮታው በሰጣቸው ነገር ላይ ይመቀኛሉን ለኢብራሂምም ቤተሰቦች መጽሐፍንና ጥበብን በእርግጥ ሰጠን ታላቅንም ንግሥና ሰጠናቸው፡፡
Verse 55
ከእነሱም (ከይሁዶች) በእርሱ ያመነ አለ፡፡ ከእነርሱም ከእርሱ ያፈገፈ አለ፡፡ አቃጣይነትም በገሀነም በቃ፡፡
Verse 56
እነዚያን በተአምራታችን የካዱትን በእርግጥ እሳትን እናገባቸዋለን፡፡ ስቃይን እንዲቀምሱ ቆዳዎቻቸው በተቃጠሉ ቁጥር ሌሎችን ቆዳዎች እንለውጥላቸዋለን፡፡ አላህ አሸናፊ ጥበበኛ ነውና፡፡
Verse 57
እነዚያንም ያመኑትንና መልካም ሥራዎችን የሠሩትን ከስራቸው ወንዞች የሚፈሱባቸውን ገነቶች ዘልዓለም በውስጣቸው ዘውታሪዎች ሲኾኑ በእርግጥ እናገባቸዋለን፡፡ ለእነሱ በውስጥዋ ንጹሕ ሚስቶች አሉዋቸው፡፡ የምታስጠልልን ጥላም እናገባቸዋለን፡፡
Verse 58
አላህ አደራዎችን ወደ ባለቤቶቻቸው እንድታደርሱ ያዛችኋል፡፡ በሰዎችም መካከል በፈረዳችሁ ጊዜ በትክክል እንድትፈርዱ (ያዛችኋል)፡፡ አላህ በርሱ የሚገሥጻችሁ ነገር ምን ያምር! አላህ ሰሚ ተመልካች ነው፡፡
Verse 59
እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አላህን ተገዙ፡፡ መልክተኛውንና ከእናንተም የስልጣን ባለቤቶችን ታዘዙ፡፡ በማንኛውም ነገር ብትከራከሩ በአላህና በመጨረሻው ቀን የምታምኑ ብትኾኑ (የተከራከራችሁበትን ነገር) ወደ አላህና ወደ መልክተኛው መልሱት፡፡ ይህ የተሻለ መጨረሻውም ያማረ ነው፡፡
Verse 60
ወደ እነዚያ እነርሱ በአንተ ላይ በተወረደውና ከአንተ በፊትም በተወረደው አምነናል ወደሚሉት፤ አላየህምን በእርሱ እንዲክዱ በእርግጥ የታዘዙ ሲኾኑ ወደ ጣዖት መፋረድን ይፈልጋሉ፡፡ ሰይጣንም (ከእውነት) የራቀን መሳሳት ሊያሳስታቸው ይፈልጋል፡፡
Verse 61
ለእነርሱም፡- «አላህ ወደ አወረደው (ቁርኣን)ና ወደ መልክተኛው ኑ» በተባሉ ጊዜ መናፍቃን ከአንተ መሸሽን ሲሸሹ ታያቸዋለህ፡፡
Verse 62
እጆቻቸውም ባስቀደሙት (ጥፋት) መከራ በደረሰችባቸውና ከዚያም «ደግን ሐሳብና ማስማማትን እንጅ ሌላ አልሻንም» በማለት በአላህ የሚምሉ ኾነው በመጡህ ጊዜ እንዴት ይኾናሉ
Verse 63
እነዚህ እነዚያ አላህ በልቦቻቸው ውስጥ ያለውን ሁሉ የሚያውቅባቸው ናቸው፡፡ እነርሱንም ተዋቸው ገሥጻቸውም፡፡ ለእነርሱም በነፍሶቻቸው ውስጥ ስሜት ያለውን ቃል ተናገራቸው፡፡
Verse 64
ማንንም መልክተኛ በአላህ ፈቃድ ሊታዘዙት እንጅ አልላክንም፡፡ እነሱም ነፍሶቻቸውን በበደሉ ጊዜ ወደ አንተ ቢመጡና አላህንም ምሕረትን በለመኑ መልክተኛውም ለነርሱ ምሕረትን በለመነላቸው ኖሮ አላህን ጸጸትን ተቀባይ አዛኝ ኾኖ ባገኙት ነበር፡፡
Verse 65
በጌታህም እምላለሁ በመካከላቸው በተከራከሩበት ፍርድ እስከሚያስፈርዱህ ከዚያም ከፈረድከው ነገር በነፍሶቻቸው ውስጥ ጭንቀትን እስከማያገኙና ፍጹም መታዘዝንም እስከሚታዘዙ ድረስ አያምኑም፤ (ምእመን አይኾኑም)፡፡
Verse 66
እኛም በእነርሱ ላይ፡- «ነፍሶቻችሁን ግደሉ ወይም ከአገሮቻችሁ ውጡ» ማለትን በጻፍን ኖሮ ከነሱ ጥቂቶቹ እንጅ ባልሠሩት ነበር፡፡ እነርሱም በእርሱ የሚገሰጹበትን ነገር በሠሩ ኖሮ ለነሱ መልካምና (በእምነታቸው ላይ) ለመርጋትም በጣም የበረታ በኾነ ነበር፡፡
Verse 67
ﭮﭯﭰﭱﭲﭳ
ﭴ
ያን ጊዜም ከእኛ ዘንድ ታላቅን ምንዳ በሰጠናቸው ነበር፡፡
Verse 68
ﭵﭶﭷ
ﭸ
ቀጥተኛውንም መንገድ በእርግጥ በመራናቸው ነበር፡፡
Verse 69
አላህንና መልክተኛውንም የሚታዘዝ ሰው እነዚያ ከእነዚያ አላህ በእነርሱ ላይ ከለገሳቸው ከነቢያት፣ ከጻድቃንም፣ ከሰማዕታትም፣ ከመልካሞቹ ጋር ይኾናሉ፡፡ የእነዚያም ጓደኝነት አማረ፡፡
Verse 70
ይህ ችሮታ ከአላህ ነው፡፡ አዋቂነትም በአላህ በቃ፡፡
Verse 71
እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ጥንቃቄያችሁን ያዙ፡፡ ክፍልፍልም Ñድ ሆናችሁ (ለዘመቻ) ውጡ፡፡ ወይም ተሰብስባችሁ ውጡ፡፡
Verse 72
ከእናንተም ውስጥ በእርግጥ (ከዘመቻ) ወደ ኋላ የሚንጓደድ ሰው አልለ፡፡ አደጋም ብታገኛችሁ ከእነሱ ጋር ተጣጅ ባልኾንኩ ጊዜ አላህ በእኔ ላይ በእርግጥ ለገሰልኝ ይላል፡፡
Verse 73
ከአላህም የኾነ ችሮታ ቢያገኛችሁ በእናንተና በእርሱ መካከል ፍቅር እንዳልነበረች ሁሉ «ታላቅ ዕድልን አገኝ ዘንድ ከነሱ ጋር በኾንኩ ወይ ምኞቴ!» ይላል፡፡
Verse 74
እነዚያም ቅርቧን ሕይወት በመጨረሻይቱ ሕይወት የሚለውጡ በአላህ መንገድ ይጋደሉ፡፡ በአላህም መንገድ የሚጋደል፣ የሚገደልም ወይም የሚያሸንፍ ታላቅ ምንዳን በእርግጥ እንሰጠዋለን፡፡
Verse 75
በአላህ መንገድና ከወንዶች ከሴቶችና ከልጆችም የኾኑትን ደካሞች እነዚያን፡- «ጌታችን ሆይ! ከዚች ባለቤቶችዋ በዳይ ከኾኑት ከተማ አውጣን ከአንተም ዘንድ ለእኛ አሳዳሪን አድርግልን ከአንተ ዘንድም ለእኛ ረዳትን አድርግልን» የሚሉትን (ለማዳን) የማትጋደሉት ለእናንተ ምን አላችሁ
Verse 76
እነዚያ ያመኑት ሰዎች በአላህ መንገድ ይጋደላሉ፡፡ እነዚያ የካዱትም በጣዖት መንገድ ይጋደላሉ፡፡ የሰይጣንንም ጭፍሮች ተጋደሉ፡፡ የሰይጣን ተንኮል ደካማ ነውና፡፡
ወደእነዚያ ለእነርሱ፡- እጆቻችሁን (ከመጋደል) ሰብስቡ፣ ሶላትንም ደንቡን ጠብቃችሁ ስገዱ፣ ግዴታ ምጽዋትም ስጡ ወደ ተባሉት አላየህምን በእነርሱም ላይ መጋደል በተጻፈ ጊዜ ከእነሱ ከፊሎቹ ወዲያውኑ ሰዎችን አላህን እንደሚፈሩ ወይም የበለጠ ፍራቻን ይፈራሉ፡፡ «ጌታችን ሆይ! በእኛ ላይ መጋደልን ለምን ደነገግክ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ አታቆየንም ኖሮአልን» ይላሉም፡፡ «የቅርቢቱ ሕይወት ጥቅም አነስተኛ ነው፡፡ መጨረሻይቱም ዓለም አላህን ለሚፈራ ሰው በላጭ ናት፡፡ በተምር ፍሬ ውስጥ ያለን ክር ያህል እንኳ አትበደሉም» በላቸው፡፡
Verse 78
«የትም ስፍራ ብትኾኑ በጠነከሩ ሕንጻዎች ውስጥ ብትኾኑም እንኳ ሞት ያገኛችኋል፡፡ ደግም ነገር ብታገኛቸው ይህች ከአላህ ዘንድ ናት» ይላሉ፡፡ መከራም ብታገኛቸው «ይህቺ ከአንተ ዘንድ ናት» ይላሉ፡፡ «ሁሉም (ደጉም ክፉውም) ከአላህ ዘንድ ነው» በላቸው፡፡ ለእነዚህም ሰዎች ንግግርን ሊረዱ የማይቀርቡት ምን አላቸው
Verse 79
ከደግ ነገር የሚያገኝህ ከአላህ (ችሮታ) ነው፡፡ ከመከራም የሚደርስብህ ከራስህ (ጥፋት የተነሳ) ነው፡፡ ለሰዎችም ሁሉ መልክተኛ ኾነህ ላክንህ፡፡ መስካሪም በአላህ በቃ፡፡
Verse 80
መልክተኛውን የሚታዘዝ ሰው በእርግጥ አላህን ታዘዘ፡፡ ከትእዛዝም የሸሸ ሰው (አያሳስብህ)፡፡ በእነሱ ላይ ጠባቂ አድርገን አልላክንህምና፡፡
Verse 81
«(ነገራችን) መታዘዝ ነው» ይላሉም፤ ከአንተም ዘንድ በወጡ ጊዜ ከነርሱ ከፊሎቹ ከዚያ (በፊትህ) ከሚሉት ሌላን (በልቦቻቸው) ያሳድራሉ፡፡ አላህም የሚያሳድሩትን ነገር ይጽፋል፡፡ ስለዚህ ተዋቸው፡፡ በአላህም ላይ ተጠጋ፡፡ መጠጊያም በአላህ በቃ፡፡
Verse 82
ቁርኣንን አያስተነትኑምን ከአላህ ሌላ ዘንድ በነበረ ኖሮ በርሱ ውስጥ ብዙን መለያየት ባገኙ ነበር፡፡
Verse 83
ከጸጥታ ወይም ከፍርሃት አንዳች (ወሬ) በመጣላቸውም ጊዜ እርሱን ያጋንናሉ፡፡ ወደ መልክተኛውና ከእነርሱ ወደ ትዕዛዙ ባለቤቶች (ወደ ዐዋቂዎቹ) በመለሱት ኖሮ እነዚያ ከእነርሱ (ነገሩን) የሚያውጣጡት ባወቁት ነበር፡፡ በእናንተም ላይ የአላህ ችሮታና እዝነቱ ባልነበረ ኖሮ ከጥቂቶች በስተቀር ሰይጣንን በተከተላችሁ ነበር፡፡
Verse 84
በአላህም መንገድ ተጋደል፡፡ ራስህን እንጅ ሌላን አትገደድም፡፡ ምእምናንንም (በመጋደል ላይ) አደፋፍር፡፡ አላህ የእነዚያን የካዱትን ኀይል ሊከለክል ይከጀላል፡፡ አላህም በኀይል በመያዙ የበረታ ቅጣቱም የጠነከረ ነው፡፡
Verse 85
መልካም መታደግን የሚታደግ ሰው ለእርሱ ከርስዋ ዕድል ይኖረዋል፡፡ መጥፎ መታደግንም የሚታደግ ሰው ለእርሱ ከርስዋ ድርሻ ይኖረዋል፡፡ አላህ በነገሩ ሁሉ ላይ ቻይ ነው፡፡
Verse 86
በሰላምታ በተከበራችሁም ጊዜ ከእርሷ ይበልጥ ባማረ (ሰላምታ) አክብሩ፡፡ ወይም (እርሷኑ) መልሷት፡፡ አላህ በነገሩ ሁሉ ላይ ተቆጣጣሪ ነውና፡፡
Verse 87
አላህ ከእርሱ በስተቀር አምላክ የለም፡፡ ወደ ትንሣኤ ቀን በርሱ ጥርጥር የሌለበት ሲኾን በእርግጥ ይሰበስባችኋል፡፡ በንግግርም ከአላህ ይበልጥ እውነተኛ ማነው
Verse 88
በመናፍቃንም (ነገር) አላህ በሥራዎቻቸው ወደ ክህደት የመለሳቸው ሲኾኑ ሁለት ክፍሎች የኾናችሁት ለናንተ ምን አላችሁ አላህ ያጠመመውን ሰው ልታቀኑ ታስባላችሁን አላህም ያሳሳተውን ሰው ለእርሱ መንገድን ፈጽሞ አታገኝለትም፡፡
Verse 89
(እነርሱ) እንደ ካዱ ብትክዱና እኩል ብትኾኑ ተመኙ! በአላህም ሃይማኖት እስከሚሰደዱ ድረስ ከነሱ ወዳጆችን አትያዙ፡፡ (ከእምነት) ቢያፈገፍጉም ያዙዋቸው፤ (ማርኩዋቸው)፡፡ ባገኛችሁበትም ስፍራ ግደሉዋቸው፡፡ ከእነሱም ወዳጅንና ረዳትን አትያዙ፡፡
Verse 90
እነዚያ በእናንተና በእነርሱ መካከል ቃል ኪዳን ወዳላቸው ሕዝቦች የሚጠጉና ወይም እናንተን ለመጋደል ወይም ወገኖቻቸውን ለመጋደል ልቦቻቸው የተጨነቁ ኾነው የመጧዋችሁ ሲቀሩ፤ (እነዚያንስ አትጋደሉዋቸው)፡፡ አላህም በሻ ኖሮ በእናንተ ላይ ኀይል በሰጣቸውና በተጋደሉዋችሁ ነበር፡፡ ቢተዋችሁና ባይጋደሉዋችሁም ወደ እናንተም እርቅን ቢያቀርቡ አላህ ለእናንተ በነሱ ላይ (የመጋደል) መንገድን አላደረገም፡፡
Verse 91
ሌሎች ከእናንተ ለመዳን ከወገኖቻቸውም ለመዳን የሚፈልጉን ታገኛላችሁ፡፡ ወደ እውከት እንዲመለሱ በተጠሩ ቁጥር በርሷ ውስጥ ይመለሳሉ፡፡ ባይተውዋችሁና እርቅንም ባያቀርቡላችሁ፣ እጆቻቸውንም ባይሰበስቡ፣ ባገኛችኋቸው ስፍራ ማርኩዋቸው፡፡ ግደሉዋቸውም፡፡ እነዚያንም ለእናንተ በነሱ ላይ ግልጽ ማስረጃን አድርገናል፡፡
ለምእመንም በስሕተት ካልኾነ በቀር ምእመንን መግደል አይገባውም፡፡ ምእመንንም በስህተት የገደለ ሰው ያመነችን ጫንቃ (ባሪያ) ነጻ ማውጣትና ወደ ቤተሰቦቹም የምትሰጥ ጉማ ምሕረት ካላደረጉለት በስተቀር (መክፈል) አለበት፡፡ እርሱ (ተገዳዩ) ምእመን ሲኾን ለእናንተ ጠላት ከኾኑትም ሕዝቦች ቢኾን ያመነችን ጫንቃ ነጻ ማውጣት (ብቻ) አለበት፡፡ በእናንተና በእነሱ መካከል ቃል ኪዳን ካላቸውም ሕዝቦች ቢኾን ወደ ቤተሰቦቹ በእጅ የምትሰጥ ጉማና ያመነችን ጫንቃ ነጻ ማውጣት አለበት፡፡ ያላገኘ ሰውም ተከታታዮችን ሁለት ወሮች መጾም አለበት፡፡ አላህ መጸጸትን ለመቀበል (ደነገገላችሁ)፡፡ አላህም ዐዋቂ ጥበበኛ ነው፡፡
Verse 93
ምእመንንም አስቦ የሚገድል ሰው ቅጣቱ በውስጧ ዘውታሪ ሲኾን ገሀነም ናት፡፡ አላህም በርሱ ላይ ተቆጣ፡፡ ረገመውም፡፡ ለእርሱም ከባድ ቅጣትን አዘጋጀ፡፡
Verse 94
እናንተ ያመናችሁ ሆይ! በአላህ መንገድ (ለመጋደል) በተጓዛችሁ ጊዜ አስረግጡ፡፡ ሰላምታንም ወደናንተ ላቀረበ ሰው የቅርቢቱን ሕይወት ጥቅም የምትፈልጉ ኾናችሁ ምእመን አይደለህም አትበሉ፡፡ አላህም ዘንድ ብዙ ዘረፋዎች አሉ፡፡ ከዚህ በፊት እንደዚሁ ነበራችሁ፡፡ አላህም በእናንተ ላይ ለገሰ ስለዚህ አስተውሉ፡፡ አላህ በምትሠሩት ሁሉ ውስጠ ዐዋቂ ነውና፡፡
Verse 95
ከምእመናን የጉዳት ባለቤት ከኾኑት በቀር ተቀማጮቹና በአላህ መንገድ በገንዘቦቻቸውና በነፍሶቻቸው የሚታገሉት አይተካከሉም፡፡ በገንዘቦቻቸውና በነፍሶቻቸው የሚታገሉትን አላህ በተቀማጮቹ ላይ በደረጃ አበለጠ፡፡ ለሁሉም አላህ መልካሚቱን (ገነት) ተስፋ ሰጠ፡፡ ታጋዮቹንም በተቀማጮቹ ላይ አላህ በታላቅ ምንዳ አበለጠ፡፡
Verse 96
ከእርሱ ዘንድ በኾኑ ደረጃዎች (አበለጠ)፡፡ ምሕረትንም አደረገ፡፡ እዝነትም አዘነላቸው፡፡ አላህም መሓሪ አዛኝ ነው፡፡
Verse 97
እነዚያ (ለእምንት ባለመሰደድ) ነፍሶቻቸውን በዳዮች ኾነው መላእክት (በበድር) የገደሉዋቸው (መላእክት ለነርሱ) «በምን ነገር ላይ ነበራችሁ» አሏቸው፡፡ «በምድር ውስጥ ደካሞች ነበርን» አሉ፡፡ «የአላህ ምድር ትሰደዱባት ዘንድ ሰፊ አልነበረችምን» አሉዋቸው፡፡ እነዚያም መኖሪያቸው ገሀነም ናት፡፡ በመመለሻነትም ከፋች!
Verse 98
ግን ከወንዶችና ከሴቶች ከሕፃኖችም ሲኾኑ (ለመውጣት) መላን የማይችሉና መንገድንም የማይምመሩ ደካሞች (ቅጣት የለባቸውም)
Verse 99
እነዚያም አላህ ከእነርሱ ይቅርታ ሊያደርግ ይሻል፡፡ አላህም ይቅር ባይ መሓሪ ነው፡፡
Verse 100
በአላህም መንገድ የሚሰደድ ሰው በምድር ውስጥ ብዙ መሰደጃንና ምቾትን ያገኛል፡፡ ወደ አላህና ወደ መልክተኛውም ስደተኛ ኾኖ ከቤቱ የሚወጣ ከዚያም (በመንገድ) ሞት የሚያገኘው ሰው ምንዳው በእርግጥ አላህ ዘንድ ተረጋገጠ፡፡ አላህም መሓሪ አዛኝ ነው፡፡
Verse 101
በምድርም ላይ በተጓዛችሁ ጊዜ እነዚያ የካዱት ያውኩናል ብላችሁ ብትፈሩ ከሶላት (ባለ አራት ረከዓት የኾኑትን) ብታሳጥሩ በናንተ ላይ ኀጢአት የለም፡፡ ከሓዲዎች ለእናንተ በእርግጥ ግልጽ ጠላቶች ናቸውና፡፡
በውስጣቸውም በኾንክና ሶላትን ለእነርሱ ባስገደድካቸው ጊዜ ከእነሱ አንዲት ጭፍራ ካንተ ጋር ትቁም፡፡ መሣሪያዎቻቸውንም ይያዙ፡፡ በግንባራቸውም በተደፉ ጊዜ ከስተኋላችሁ ይኹኑ፡፡ (እነዚህ ይኺዱና) ያልሰገዱትም ሌሎቹ ጭፍሮች ይምጡ፡፡ ከአንተም ጋር ይስገዱ፡፡ ጥንቃቄያቸውንና መሣሪያዎቻቸውንም ይያዙ፡፡ እነዚያ የካዱት ከመሣሪያዎቻችሁና ከጓዞቻችሁ ብትዘነጉና በእናንተ ላይ አንዲትን መዘንበል ቢዘነበሉ ተመኙ፡፡ ከዝናብም የኾነ ችግር በእናንተ ቢኖር ወይም ሕመምተኞች ብትኾኑ መሣሪያዎቻችሁን ብታስቀምጡ በናንተ ላይ ኀጢአት የለም፡፡ ጥንቃቄያችሁንም ያዙ፡፡ አላህ ለከሓዲዎች አዋራጅን ቅጣት አዘጋጀ፡፡
Verse 103
ሶላትንም በፈጸማችሁ ጊዜ ቆማችሁም ተቀምጣችሁም በጎኖቻችሁም ላይ ተጋድማችሁ አላህን አውሱ፡፡ በረጋችሁም ጊዜ ሶላትን (አሟልታችሁ) ስገዱ፡፡ ሶላት በምእምናን ላይ በጊዜያት የተወሰነች ግዴታ ናትና፡፡
Verse 104
ሰዎቹንም በመፈለግ አትስነፉ፡፡ (ስትቆስሉ) የምትታመሙ ብትኾኑ እናንተ እንደምትታመሙ እነሱም ይታመማሉ፡፡ የማይከጅሉትንም ከአላህ ትከጅላላችሁ፡፡ አላህም ዐዋቂ ጥበበኛ ነው፡፡
Verse 105
እኛ በሰዎች መካከል አላህ ባሳወቀህ ልትፈርድ ወደ አንተ መጽሐፉን በእውነት አወረድን፡፡ ለከዳተኞችም ተከራካሪ አትኹን፡፡
Verse 106
አላህንም ምሕረትን ለምን፡፡ አላህ መሓሪ አዛኝ ነውና፡፡
Verse 107
ከእነዚያም ነፍሶቻቸውን ከሚበድሉት ላይ አትከራከር፡፡ አላህ ከዳተኛ ኃጢአተኛ የኾነን ሰው አይወድምና፡፡
Verse 108
ከሰው ይደበቃሉ፡፡ አላህም እርሱ (በዕውቀቱ) ከእነሱ ጋር ሲኾን ከንግግር የማይወደውን ነገር (በልቦቻቸው) በሚያሳድሩ ጊዜ (ከእርሱ) አይደበቁም፡፡ አላህም በሚሠሩት ሁሉ (በዕውቀቱ) ከባቢ ነው፡፡
Verse 109
እነሆ እናንተ እነዚያ በቅርቢቱ ሕይወት ከነሱ የተከራከራችሁ ናችሁ፡፡ በትንሣኤ ቀን አላህን ስለእነሱ የሚከራከር ማን ነው ወይስ ለእነሱ ኃላፊና መመኪያ የሚኾን ማን ነው
Verse 110
መጥፎም የሚሠራ ሰው ወይም ነፍሱን የሚበድል ከዚያም (ተጸጽቶ) አላህን ምሕረት የሚለምን አላህን መሓሪ አዛኝ ኾኖ ያገኘዋል፡፡
Verse 111
ኀጢአትንም የሚሠራ ሰው የሚሠራው ጥፋት በራሱ ላይ ነው፡፡ አላህም ዐዋቂ ጥበበኛ ነው፤
Verse 112
ኀጢአትን ወይም አበሳን የሚሠራም ሰው ከዚያም በእርሱ ንጹሕን ሰው የሚሰድብ ቅጥፈትንና ግልጽ አበሳን በቁርጥ ተሸከመ፡፡
Verse 113
የአላህም ችሮታና እዝነቱ ባንተ ላይ ባልነበረ ኖሮ ከእነሱ የኾኑ ጭፍሮች ሊያሳስቱህ ባሰቡ ነበር፡፡ ነፍሶቻቸውንም እንጅ ሌላን አያሳስቱም፡፡ በምንም አይጐዱህም፡፡ አላህም በአንተ ላይ መጽሐፍንና ጥበብን አወረደ፡፡ የማታውቀውንም ሁሉ አስተማረህ፡፡ የአላህም ችሮታ በአንተ ላይ ታላቅ ነው፡፡
Verse 114
ከውይይታቸው በምጽዋት ወይም በበጎ ሥራ ወይም በሰዎች መካከል በማስታረቅ ከሚያዙ ሰዎች ውይይት በስተቀር በብዙው ውስጥ ደግ ነገር የለበትም፡፡ ይኸንንም (የተባለውን) የአላህን ውዴታ ለመፈለግ የሚሠራ ሰው ታላቅ ምንዳን እንሰጠዋለን፡፡
Verse 115
ቅኑም መንገድ ለእርሱ ከተገለጸ በኋላ መልክተኛውን የሚጨቃጨቅና ከምእምኖቹ መንገድ ሌላ የኾነን የሚከተል ሰው (በዚህ ዓለም) በተሾመበት (ጥመት) ላይ እንሾመዋለን፤ ገሀነምንም እናገባዋለን፡፡ መመለሻይቱም ከፋች!
Verse 116
አላህ በርሱ የማጋራትን (ወንጀል) አይምርም፡፡ ከዚህም ወዲያ ያለውን ለሚሻው ሰው ይምራል፡፡ በአላህም የሚያጋራ ሰው (ከእውነት) የራቀን መሳሳት በእርግጥ ተሳሳተ፡፡
Verse 117
ከእርሱ ሌላ እንስታትን እንጅ አይገዙም፡፡ አመጸኛ ሰይጣንንም እንጅ ሌላን አይግገዙም፡፡
Verse 118
«አላህ የረገመውን ከባሮችህም የተወሰነን ድርሻ በእርግጥ እይዛለሁ» ያለውን (ሰይጣን እንጅ ሌላን አይከተሉም)፡፡
Verse 119
በእርግጥ አጠማቸዋለሁም፡፡ (ከንቱን) አስመኛቸዋለሁም፡፡ አዛቸውምና የእንስሶችን ጆሮዎች ይተለትላሉ፡፡ አዛቸውምና የአላህን ፍጥረት ይለውጣሉ፤ (ያለውን ይከተላሉ)፡፡ ከአላህም ሌላ ሰይጣንን ረዳት አድርጎ የሚይዝ ሰው ግልጽ ክስረትን በአርግጥ ከሰረ፡፡
Verse 120
(የማይፈጸመውን) ተስፋ ይሰጣቸዋል፡፡ ያስመኛቸዋልም፡፡ ሰይጣንም ለማታለል እንጅ አይቀጥራቸውም፡፡
Verse 121
እነዚያ መኖሪያቸው ገሀነም ናት፡፡ ከርስዋም መሸሻን አያገኙም፡፡
Verse 122
እነዚያም ያመኑና በጎ ሥራዎችን የሠሩ በሥራቸው ወንዞች የሚፈሱባቸውን ገነቶች ዘላለም በውስጣቸው ዘውታሪዎች ሲኾኑ እናገባቸዋለን፡፡ አላህ እውነተኛን ተስፋ ሰጣቸው፡፡ በንግግርም ከአላህ ይበልጥ እውነተኛ ማን ነው
Verse 123
(ነገሩ) በምኞታችሁና በመጽሐፉ ሰዎች ምኞት አይደለም፡፡ መጥፎን የሚሠራ ሰው በእርሱ ይቀጣል፡፡ ለእርሱም ከአላህ ሌላ ጠባቂንም ረዳትንም አያገኝም፡፡
Verse 124
ከወንድ ወይም ከሴት እርሱ አማኝ ኾኖ ከበጎ ሥራዎች አንዳችን የሚሠራም ሰው እነዚያ ገነትን ይገባሉ፡፡ በተምር ፍሬ ላይ ያለችን ነጥብ ያክል እንኳ አይበደሉም፡፡
Verse 125
እርሱ መልካም ሠሪ ኾኖ ፊቱን ለአላህ ከሰጠና የኢብራሂምንም መንገድ ቀጥተኛ ሲኾን ከተከተለ ሰው ይበልጥ ሃይማኖቱ ያማረ ማን ነው አላህም ኢብራሂምን ፍጹም ወዳጅ አድርጐ ያዘው፡፡
Verse 126
በሰማያት ያለውና በምድር ያለው ሁሉ የአላህ ነው፡፡ አላህም በነገሩ ሁሉ በዕውቀት ከባቢ ነው፡፡
Verse 127
በሴቶችም ነገር ያስተቹሃል፡፡ አላህ በእነርሱ ይነግራችኋል፡፡ ያም በመጽሐፉ በእናንተ ላይ የሚነበበው በእነዚያ ለእነርሱ (ከውርስ) የተጻፈላቸውን በማትሰጧቸውና ልታገቧቸው በማትፈልጉት የቲሞች ሴቶች (ይህንን እንዳታደርጉ) ከሕፃናትም ለኾኑት ደካሞች መብታቸውን እንድትሰጡ ለየቲሞችም በትክክል አንድትቆሙ (ይነግራችኋል) በላቸው፡፡ ከበጎም ሥራ ማናቸውንም ብትሠሩ አላህ እርሱን ዐዋቂ ነው፡፡
Verse 128
ሴትም ከባልዋ ጥላቻን ወይም ፊቱን ማዞርን ብታውቅ በመካከላቸው መስማማትን ቢስማሙ በሁለቱ ላይ ኀጢአት የለም፡፡ መታረቅም መልካም ነው፡፡ ነፍሶችም ንፍገት ተጣለባቸው፡፡ መልካምም ብትሠሩ ብትጠነቀቁም አላህ በምትሠሩት ሁሉ ውስጠ ዐዋቂ ነው፡፡
Verse 129
በሴቶችም መካከል ምንም እንኳ ብትጓጉ (በፍቅር) ለማስተካከል አትችሉም፡፡ እንደ ተንጠለጠለችም አድርጋችሁ ትተዋት ዘንድ (ወደምትወዷት) መዘንበልን ሁሉ አትዘንበሉ፡፡ ብታበጁም ብትጠነቀቁም አላህ መሓሪ አዛኝ ነው፡፡
Verse 130
ቢለያዩም አላህ ሁሉንም በችሮታው ያብቃቃቸዋል፡፡ አላህም ችሮታው ሰፊ ጥበበኛ ነው፡፡
Verse 131
በሰማያት ያለውና በምድርም ያለው ሁሉ የአላህ ነው፡፡ እነዚያንም ከበፊታችሁ መጽሐፍን የተሰጡትን እናንተንም አላህን ፍሩ በማለት በእርግጥ አዘዝን፡፡ ብትክዱም በሰማያትና በምድር ያለው ሁሉ የአላህ ነው፡፡ (አትጐዱትም)፡፡ አላህም ተብቃቂ ምስጉን ነው፡፡
Verse 132
በሰማያት ያለውና በምድርም ያለው ሁሉ የአላህ ነው፡፡ መመከያም በአላህ በቃ፡፡
Verse 133
ሰዎች ሆይ!(አላህ) ቢሻ ያስወግዳችኋል፡፡ ሌሎችንም ያመጣል፡፡ አላህም በዚህ ላይ ቻይ ነው፡፡
Verse 134
የቅርቢቱን ዓለም ምንዳ የሚፈልግ የኾነ ሰው አላህ ዘንድ የቅርቢቱና የመጨረሻይቱ ምንዳ አልለ፡፡ አላህም ሰሚ ተመልካች ነው፡፡
Verse 135
እናንተ ያመናችሁ ሆይ! በትክክል (ፍትሕ) ቀዋሚዎች በነፈሶቻችሁ ወይም በወላጆችና በቅርብ ዘመዶች ላይ ቢኾንም እንኳ ለአላህ መስካሪዎች ኹኑ፡፡ ሀብታም ወይም ድኻ ቢኾን አላህ በእነርሱ (ከእናንተ) ይበልጥ ተገቢ ነው፡፡ እንዳታደሉም ዝንባሌን አትከተሉ፡፡ ብታጠምሙም ወይም (መመስከርን) ብትተው አላህ በምትሠሩት ሁሉ ውስጠ ዐዋቂ ነው፡፡
Verse 136
እናንተ ያመናችሁ ሆይ! በአላህና በመልክተኛው በዚያም በመልክተኛው ላይ ባወረደው መጽሐፍ በዚያም ከበፊቱ ባወረደው መጽሐፍ እመኑ፡፡ በአላህና በመላእክቱም፣ በመጽሐፎቹም፣ በመልክተኞቹም፣ በመጨረሻውም ቀን፣ የካደ ሰው (ከእውነት) የራቀን መሳሳት በእርግጥ ተሳሳተ፡፡
Verse 137
እነዚያ (በሙሳ) ያመኑና ከዚያም (ወይፈንን በመገዛት) የካዱ ከዚያም (በእርሱ) ያመኑ ከዚያም (በዒሳ) የካዱ ከዚያም (በሙሐመድ) ክሕደትን የጨመሩ አላህ ለእነሱ የሚምራቸውና ቅኑን መንገድ የሚመራቸው አይደለም፡፡
Verse 138
ﮮﮯﮰﮱﯓﯔ
ﯕ
መናፍቃንን ለእነርሱ አሳማሚ ቅጣት ያላቸው መኾኑን አብስራቸው፡፡
Verse 139
እነዚያ ከምእምናን ሌላ ከሓዲዎችን ወዳጆች አድርገው የሚይዙ እነሱ ዘንድ ልቅናን ይፈልጋሉን ልቅናውም ሁሉ ለአላህ ብቻ ነው፡፡
Verse 140
በእናንተም ላይ በመጽሐፉ ውስጥ የአላህን አንቀጾች በርሷ ሲካድባትና በርሷም ሲላገጥባት በሰማችሁ ጊዜ በሌላ ወሬ ውስጥ እስከሚገቡ ድረስ ከእነሱ ጋር አትቀመጡ፡፡ ማለትን በእርግጥ አወረደ፡፡ እናንተ ያንጊዜ ብጤያቸው ናችሁና፡፡ አላህ መናፍቃንን እና ከሓዲዎችን በሙሉ በገሀነም ውስጥ ሰብሳቢ ነውና፡፡
Verse 141
እነዚያ በእናንተ (የጊዜን መዘዋወር) የሚጠባበቁ ናቸው፡፡ ለእናንተም ከአላህ የኾነ አሸናፊነት «ቢኖራችሁ ከእናንተ ጋር አልነበርንምን» ይላሉ፡፡ ለከሓዲዎችም ዕድል ቢኖር «(ከአሁን በፊት) በእናንተ ላይ አልተሾምንምን (እና አልተውናችሁምን) ከምእምናንም (አደጋ) አልከለከልናችሁምን» ይላሉ፡፡ አላህም በትንሣኤ ቀን በመካከላችሁ ይፈርዳል፡፡ አላህም ለከሓዲዎች በምእምናን ላይ መንገድን በፍጹም አያደርግም፡፡
Verse 142
መናፍቃን አላህን ያታልላሉ፡፡ እርሱም አታላያቸው ነው፡፡ (ይቀጣቸዋል)፡፡ ወደ ሶላትም በቆሙ ጊዜ ታካቾች ስዎችን የሚያሳዩ ኾነው ይቆማሉ፡፡ አላህንም ጥቂትን እንጅ አያወሱም፡፡
Verse 143
በዚህ መካከል ወላዋዮች ኾነው (ያሳያሉ)፡፡ ወደእነዚህም ወደእነዚያም አይደሉም፡፡ አላህም ያሳሳተውን ሰው ለእርሱ (የቅንነት) መንገድን በፍፁም አታገኝለትም፡፡
Verse 144
እናንተ ያመናችሁ ሆይ! ከምእምናን ሌላ ከሓዲዎችን ወዳጆች አድርጋችሁ አትያዙ፤ ለአላህ በናንተ ላይ ግልጽ ማስረጃዎችን ልታደርጉ ትፈልጋላችሁን
Verse 145
መናፍቃን በእርግጥ ከእሳት በታችኛው አዘቅት ውስጥ ናቸው፡፡ ለእነሱም ረዳትን አታገኝላቸውም፡፡
Verse 146
እነዚያ የተመለሱ (ሥራቸውን) ያሳመሩም፤ በአላህም የተጠበቁ፤ ሃይማኖታቸውንም ለአላህ ፍጹም ያደረጉ ሲቀሩ፡፡ እነዚያስ ከምእምናን ጋር ናቸው፡፡ ለምእምናንም አላህ ታላቅን ምንዳ በእርግጥ ይሰጣል፡፡
Verse 147
ብታመሰግኑና ብታምኑ አላህ እናንተን በመቅጣት ምን ያደርጋል አላህም ወረታን መላሽ ዐዋቂ ነው፡፡
Verse 148
አላህ ከንግግር በክፉው መጮህን ከተበደለ ሰው (ጩኸት) በቀር አይወድም፡፡ አላህ ሰሚ ዐዋቂ ነው፡፡
Verse 149
ደግ ነገርን ብትገልጹ ወይም ብትደብቁት ወይም ከመጥፎ ነገር (ከበደል) ይቅርታ ብታደርጉ አላህ ይቅር ባይ ኃያል ነው፡፡
Verse 150
እነዚያ በአላህና በመልክተኞቹ የሚክዱ፣ በአላህና በመልክተኞቹም መካከል መለየትን የሚፈልጉ፣ «በከፊሉም እናምናለን በከፊሉም እንክዳለን» የሚሉ፣ በዚህም መካከል መንገድን ሊይዙ የሚፈልጉ፤
Verse 151
እነዚያ በውነት ከሓዲዎቹ እነርሱ ናቸው፡፡ ለከሓዲዎችም አዋራጅን ቅጣት አዘጋጅተናል፡፡
Verse 152
እነዚያም በአላህና በመልክተኞቹ ያመኑ ከነርሱም በአንድም መካከል ያልለዩ እነዚያ ምንዳዎቻቸውን በእርግጥ ይሰጣቸዋል፡፡ አላህም መሓሪ አዛኝ ነው፡፡
Verse 153
የመጽሐፉ ሰዎች በነሱ ላይ ከሰማይ መጽሐፍን እንድታወርድ ይጠይቁሃል፡፡ ከዚያም የከበደን (ነገር) ሙሳን በእርግጥ ጠይቀዋል፡፡ «አላህንም በግልጽ አሳየን» ብለዋል፡፡ በበደላቸውም መብረቅ ያዘቻቸው፡፡ ከዚያም ተዓምራቶች ከመጡላቸው በኋላ ወይፈኑን (አምላክ አድርገው) ያዙ፡፡ ከዚያም ይቅር አልን፡፡ ሙሳንም ግልጽ ስልጣንን ሰጠነው፡፡
Verse 154
በቃል ኪዳናቸውም ምክንያት የጡርን ተራራ ከበላያቸው አነሳን፡፡ ለእነሱም «ደጃፉን አጎንባሾች ኾናችሁ ግቡ» አልን፡፡ ለእነርሱም «በሰንበት ቀን ትዕዛዝን አትተላልፉ» አልን፡፡ ከእነሱም ከባድን ቃል ኪዳን ያዝን፡፡
Verse 155
ቃል ኪዳናቸውንም በማፍረሳቸው፣ በአላህም አንቀጾች በመካዳቸው፣ ነቢያትንም ያለ አግባብ በመግደላቸውና «ልቦቻችን ሽፍኖች ናቸው» በማለታቸው ምክንያት (ረገምናቸው)፡፡ በእውነቱ በክህደታቸው ምክንያት አላህ በርሷ (በልቦቻቸወ) ላይ አተመ፡፡ ስለዚህ ጥቂትን እንጅ አያምኑም፡፡
Verse 156
ﭩﭪﭫﭬﭭﭮ
ﭯ
በመካዳቸውም በመርየም ላይ ከባድ ቅጥፈትን በመናገራቸውም ምክንያት (ረገምናቸው)፡፡
Verse 157
«እኛ የአላህን መልክተኛ የመርየምን ልጅ አልመሲሕ ዒሳን ገደልን» በማለታቸውም (ረገምናቸው)፡፡ አልገደሉትም አልሰቀሉትምም፡፡ ግን ለእነሱ (የተገደለው ሰው በዒሳ) ተመሰለ፡፡ እነዚያም በእርሱ ነገር የተለያዩት ከእርሱ (መገደል) በመጠራጠር ውስጥ ናቸው፡፡ ጥርጣሬን ከመከተል በስተቀር በእርሱ ነገር ምንም ዕውቀት የላቸውም፡፡ በእርግጥም አልገደሉትም፡፡
Verse 158
ይልቁንስ አላህ (ኢሳን) ወደርሱ አነሳው፡፡ አላህም አሸናፊ ጥበበኛ ነው፡፡
Verse 159
ከመጽሐፉም ሰዎች ከመሞቱ በፊት በእርሱ (በዒሳ) በእርግጥ የሚያምን እንጅ (አንድም) የለም፡፡ በትንሣኤም ቀን በነሱ ላይ መስካሪ ይኾናል፡፡
Verse 160
ከእነዚያ ይሁዳውያን ከኾኑትም በተገኘው በደል ሰዎችንም ከአላህ መንገድ በብዙ በመከልከላቸው ምክንያት ለእነሱ ተፈቅደው የነበሩትን ጣፋጮች ምግቦች በእነርሱ ላይ እርም አደረግንባቸው፡፡
Verse 161
ከእርሱ በቁርጥ የተከለከሉ ሲኾኑ አራጣንም በመያዛቸውና የሰዎችን ገንዘቦች ያለ አግባብ (በጉቦ) በመብላታቸውም ምክንያት (የተፈቀደላቸውን እርም አደረግንባቸው)፡፡ ከእነሱም ለከሓዲዎቹ አሳማሚን ቅጣት አዘጋጀን፡፡
Verse 162
ግን ከነርሱ ውስጥ በዕውቀት የጠለቁትና ምእምናኖቹ በአንተ ላይ በተወረደውና ከአንተም በፊት በተወረደው መጽሐፍ የሚያምኑ ሲኾኑ ሶላትንም ደንቡን ጠብቀው ሰጋጆችን (እናመሰግናለን)፡፡ ዘካንም ሰጪዎቹ በአላህና በመጨረሻዎቹም ቀን አማኞቹ እነዚያ ታላቅ ምንዳን በእርግጥ እንሰጣቸዋለን፡፡
Verse 163
እኛ ወደ ኑሕና ከርሱ በኋላ ወደ ነበሩት ነቢያት እንዳወረድን ወደ አንተም አወረድን፡፡ ወደ ኢብራሂምም፣ ወደ ኢስማዒልም፣ ወደ ኢስሓቅም፣ ወደ ያዕቆብም፣ ወደ ነገዶቹም፣ ወደ ዒሳም፣ ወደ አዩብም፣ ወደ ዩኑስም፣ ወደ ሃሩንና፣ ወደ ሱለይማንም አወረድን፡፡ ለዳውድም ዘቡርን ሰጠነው፡፡
Verse 164
ከዚህም በፊት በአንተ ላይ በእርግጥ የተረክናቸውን መልክተኞች ባንተ ላይም ያልተረክናቸውን መልክተኞች (እንደላክን ላክንህ)፡፡ አላህም ሙሳን ማነጋገርን አነጋገረው፡፡
Verse 165
ከመልክተኞቹ በኋላ ለሰዎች በአላህ ላይ አስረጅ እንዳይኖር አብሳሪዎችና አስፈራሪዎች የኾኑን መልክተኞች (ላክን)፡፡ አላህም አሸናፊ ጥበበኛ ነው፡፡
Verse 166
ግን አላህ ባንተ ላይ ባወረደው ይመሰክራል፡፡ በዕውቀቱ አወረደው፡፡ መላእክቱም ይመሰክራሉ፡፡ መስካሪም በአላህ በቃ፡፡
Verse 167
እነዚያ የካዱት ከአላህም መንገድ ያገዱት (ከእውነት) የራቀን መሳሳት በእርግጥ ተሳሳቱ፡፡
Verse 168
እነዚያ የካዱ የበደሉም አላህ የሚምራቸውና (ቅን) መንገድን የሚመራቸው አይደለም፡፡
Verse 169
ግን በውስጧ ዘለዓለም ዘውታሪዎች ሲኾኑ የገሀነምን መንገድ (ይመራቸዋል)፡፡ ይህም በአላህ ላይ ገር ነው፡፡
Verse 170
እናንተ ሰዎች ሆይ! መልክተኛው እውነትን ከጌታችሁ አመጣላችሁ፡፡ እመኑም ለናንተ የተሻለ (ይኾናል)፡፡ ብትክዱም (አትጐዱትም)፡፡ በሰማያትና በምድር ያለው ሁሉ የአላህ ነውና፡፡ አላህም ዐዋቂ ጥበበኛ ነው፡፡
እናንተ የመጽሐፉ ሰዎች ሆይ! በሃይማኖታችሁ ወሰንን አትለፉ፡፡ በአላህም ላይ እውነትን እንጅ አትናገሩ፡፡ የመርየም ልጅ አልመሲሕ ዒሳ የአላህ መልክተኛ ወደ መርየም የጣላት «የኹን» ቃሉም ከእርሱ የኾነ መንፈስም ብቻ ነው፡፡ በአላህና በመልክተኞቹም እመኑ፡፡ « (አማልክት) ሦስት ናቸው» አትበሉም፡፡ ተከልከሉ፤ ለእናንተ የተሻለ ይኾናልና፡፡ አላህ አንድ አምላክ ብቻ ነው፡፡ ለእርሱ ልጅ ያለው ከመኾን የጠራ ነው፡፡ በሰማያትና በምድር ያለ ሁሉ የርሱ ነው፡፡ መመኪያም በአላህ በቃ፡፡
Verse 172
አልመሲሕ (ኢየሱስ) ለአላህ ባሪያ ከመኾን ፈጽሞ አይጠየፍም፡፡ ቀራቢዎች የኾኑት መላእክትም (አይጠየፉም)፡፡ እርሱን ከመገዛት የሚጠየፍና የሚኮራም ሰው (አላህ) ሁሉንም ወደ እርሱ በእርግጥ ይሰበስባቸዋል፡፡
Verse 173
እነዚያማ ያመኑት መልካሞችንም የሠሩት ምንዳዎቻቸውን ይሞላላቸዋል፡፡ ከችሮታውም ይጨምርላቸዋል፡፡ እነዚያን የተጠየፉትንና የኮሩትንማ አሳማሚን ቅጣት ይቀጣቸዋል፡፡ ከአላህም ሌላ ለእነሱ ዝምድንና ረዳትን አያገኙም፡፡
Verse 174
እናንተ ሰዎች ሆይ! ከጌታችሁ ዘንድ በእርግጥ አስረጅ መጣላችሁ፤ ወደእናንተም ገላጭ የኾነን ብርሃን (ቁርኣንን) አወረድን፡፡
Verse 175
እነዚያማ በአላህ ያመኑ በርሱም የተጠበቁ ከሱ በኾነው እዝነትና ችሮታ ውስጥ በእርግጥ ያስገባቸዋል፡፡ ወደእርሱም ቀጥተኛ መንገድን ይመራቸዋል፡፡
ይጠይቁሃል በላቸው፡- «ወላጅና ልጅ ሳይኖረው በሚወረስ ሰው አላህ ይነግራችኋል፡፡ ለእርሱ ልጅ የሌለው ሰው ቢሞት ለእርሱም እኅት ብትኖረው ለእርስዋ ከተወው ረጀት ግማሹ አላት፡፡ እርሱም ለርሷ ልጅ የሌላት እንደኾነች (በሙሉ) ይወርሳታል፡፡ ሁለት (እኅቶች ወይም ከሁለት በላይ) ቢኾኑም ከተወው ረጀት ከሦስት ሁለት እጁ አላቸው፡፡ ወንድሞች (ና እኅቶች) ወንዶችና ሴቶች ቢኾኑም ለወንዱ የሁለት ሴቶች ድርሻ ብጤ አለው፡፡ አላህ እንዳትሳሳቱ ለእናንተ ያብራራል፡፡ አላህም በነገሩ ሁሉ ዐዋቂ ነው፡፡»
تقدم القراءة