ترجمة سورة النازعات

الترجمة الأمهرية
ترجمة معاني سورة النازعات باللغة الأمهرية من كتاب الترجمة الأمهرية .
من تأليف: محمد صادق ومحمد الثاني حبيب .

በኃይል አውጪዎች በኾኑት፤
በቀስታ መምዘዝንም መዘዦች በኾኑት፤
መዋኘትም ዋኚዎች በኾኑት፤
መቅደምንም ቀዳሚዎች በኾኑት፤
ነገርንም አስተናባሪዎች በኾኑት (መላእክት) እምላለሁ፡፡ (በእርግጥ ትቀሰቀሳላችሁ)፡፡
ተርገፍጋፊይቱ (ምድር) በምትርገፈገፍበት ቀን፤
ለጣቂይቱ የምትከተላት ስትኾን (ትቀሰቀሳላችሁ)፡፡
በዚያ ቀን ልቦች ተሸባሪዎች ናቸው፡፡
ዓይኖቻቸው ተዋራጆች (አቀርቃሪዎች) ናቸው፡፡
«እኛ ወደ መጀመሪያይቱ ኹነታ ተመላሾች ነን?» ይላሉ፡፡
«የበሰበሱ አጥንቶች በኾን ጊዜ (እንቀሰቀሳለን?)»
«ይህቺ ያን ጊዜ ባለ ከሳራ መመለስ ናት» ይላሉ፡፡
እርሷም አንዲት ጩኸት ብቻ ናት፡፡
ወዲያውኑም እነርሱ እንቅልፍ በሌለባት (ምድር) ላይ ይኾናሉ፡፡
የሙሳ ወሬ መጣልህን?
ጌታው በተቀደሰው ሸለቆ በጡዋ በጠራው ጊዜ፤
ወደ ፈርዖን ኺድ፡፡ እርሱ ወሰን አልፏልና፡፡
በለውም፡- «ወደ መጥራራትህ ላንተ (መንገድ) አለህን?»
«ወደ ጌታህም ልመራህ ትፈራውም ዘንድ፤ (መንገድ አለህን?)» አለው፡፡
ታላቂቱንም ተዓምር አሳየው፡፡
አስተባበለም፤ አመጸም፡፡
ከዚያም (ለማጥፋት) የሚተጋ ኾኖ ዞረ፡፡
(ሰራዊቶቹን) ሰበሰበም፤ ተጣራም፡፡
አለም፡- «እኔ ታላቁ ጌታችሁ ነኝ፡፡»
አላህም በኋለኛይቱና በፊተኛይቱ (ቃል) ቅጣት ያዘው፡፡
በዚህ ውስጥ ለሚፈራ ሰው በእርግጥ መገምገሚያ አለበት፡፡
ባፈጣጠር እናንተ ይበልጥ የበረታችሁ ናችሁን? ወይንስ ሰማይ? (አላህ) ገነባት፡፡
ከፍታዋን አጓነ፤ አስተካከላትም፡፡
ሌሊቷንም አጨለመ፡፡ ቀንዋንም ገለጸ፡፡
ምድርንም ከዚህ በኋላ ዘረጋት፡፡
ውሃዋንና ግጦሿን ከእርሷ አወጣ፡፡
ጋራዎችንም አደላደላቸው፡፡
ለእናንተና ለእንስሶቻችሁ መጣቀሚያ ይኾን ዘንድ (ይህን አደረገ)፡፡
ታላቂቱም መዐት በመጣች ጊዜ፣
ሰው ሁሉ የሠራውን በሚያስታውስበት ቀን፣
ገሀነምም ለሚያይ ሰው በተገለጠች ጊዜ፣
የካደ ሰውማ፣
ቅርቢቱንም ሕይወት የመረጠ፣
ገሀነም እርሷ በእርግጥ መኖሪያው ናት፡፡
በጌታው ፊት መቆምን የፈራ ሰውማ ነፍሱንም ከዝንባሌዋ የከለከለ
ገነት እርሷ በእርግጥ መኖሪያው ናት፡፡
«ከሰዓቲቱ መቼ ነው መኾኛዋ?» ሲሉ ይጠይቁሃል፡፡
አንተ እርሷን ከማስታወስ በምን ውስጥ ነህ?
(የዕውቀት) መጨረሻዋ ወደ ጌታህ ብቻ ነው፡፡
አንተ የሚፈራትን ሰው አስፈራሪ ብቻ ነህ፡፡
እነርሱ በሚያዩዋት ቀን ያንዲት ቀን ምሽትን ወይም ረፏዷን እንጅ ያልቆዩ ይመስላሉ፡፡
Icon